09/03/2026
ሳውዲ አረቢያ የነዳጅ ምርቷን መቀነስ ጀመረች።
ለዚህ ዋነኛው ምክንያት በዓለም አቀፍ ደረጃ ለነዳጅ ዝውውር እጅግ ወሳኝ የሆነው የሆርሙዝ ሰርጥ በጦርነት ምክንያት ለመርከብ ጉዞ አስቸጋሪና ፈታኝ በመሆኑ ነው።
መካከለኛው ምስራቅ የተቀሰቀሰው ጦርነት የሆርሙዝ ሰርጥ ለንግድ መርከቦች ፈታኝ እንዲሆን አድርጎታል።
ሳውዲ አረቢያ በቀን ከ7 ሚሊዮን በርሜል በላይ ነዳጅ ለዓለም ገበያ የምትልከው በዚህ መስመር ቢሆንም አሁን ግን መርከቦች ማለፍ ባለመቻላቸው ነዳጁ ሳይላክ ተከማችቷል።
የተመረተ ነዳጅ ሚቀመጥባቸው ታንከሮች በፍጥነት እየሞሉ በመሆናቸው ምክንያት አዲስ የሚመረት ነዳጅ የሚቀመጥበት ቦታ ስለጠፋ ምርቱን ለመቀነስ ተገዳለች።
° ኩዌት፣
° የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፣
° ኢራቅም በተመሳሳይ ምክንያት ምርታቸውን ቀንሰዋል።
ሳውዲ በሆርሙዝ ሰርጥ ምትክ ነዳጇን በየብስ በኩል ወደ ቀይ ባሕር / ያንቡ ወደብ በመውሰድ ለመላክ እየሞከረች ነው ተብሏል።
ነገር ግን በዚህ በኩል ያለው የማስተላለፊያ መስመር በሰርጡ በኩል የሚላከውን ያህል ከፍተኛ መጠን የመሸከም አቅም የለውም። በዚህም ምክንያት አሁንም ከፍተኛ መጠን ያለው ነዳጅ ለገበያ መቅረብ አልቻለም።
ይህ ክስተት በዓለም ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ መናወጥ እያስከተለ ነው።
የነዳጅ ዋጋ በበርሜል ከ100 ዶላር በላይ ዘሏል።
የG7 አገራት የነዳጅ ዋጋን ለማረጋጋት የራሳቸውን የአደጋ ጊዜ ክምችት ወደ ገበያ ለማውጣት እየመከሩ ነው።
የሆርሙዝ ሰርጥ በዓለም ላይ ካለው የነዳጅ ዝውውር 20% የሚስተናገድበት ወሳኝ መስመር በመሆኑ መዘጋቱ ለረጅም ጊዜ ከቀጠለ የዓለም አቀፍ የነዳጅ እጥረት ሊባባስ ይችላል።
መረጃው የብሉምበርግ ነው።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
የካቲት 30 ቀን 2018 ዓ/ም