Wisdom Ethiopia Books

Wisdom Ethiopia Books We seek to maintain our excellence as a publisher of high quality books mostly focusing on Ethiopian history, Children and self help books.

 #ፌጦ ፍትፍትና አዲስ ዓመትበዚህ የአዲስ ዓመት ማለዳ በጠዋቱ የፌጦ ፍትፍት ቀመሳችሁ? በአብዛኛው የሀገራችን ክፍል በዚህ በዓል ቀድሞ ወደ ሆድ የሚገባው የፌጦ ፍትፍት ነው። በማለዳ ለሁሉም...
11/09/2022

#ፌጦ ፍትፍትና አዲስ ዓመት

በዚህ የአዲስ ዓመት ማለዳ በጠዋቱ የፌጦ ፍትፍት ቀመሳችሁ? በአብዛኛው የሀገራችን ክፍል በዚህ በዓል ቀድሞ ወደ ሆድ የሚገባው የፌጦ ፍትፍት ነው። በማለዳ ለሁሉም ነገር መድኃኒት ነው የሚባለው ፌጦ በእንጀራ ተፈትፍቶ ልጅ አዋቂው ሁሉ ይጎርሳል፤ በከብቶቹ ላይ፣ በማደሪያቸውና በአዝመራው ላይ የተፈተፈተው ይበተናል ወይም ፌጦው ብቻውን ተበጥብጦ ይረጫል። ይህም ፌጦ ለብዙ ሕመም መድኃኒትና ጸረ-እርኩስ መንፈስ ነው ተብሎ ስለሚታመን ነው፤ ‘ለማንኛውም ፌጦ መድኃኒት ነው’ እንዲሉ።

ቅዱስ ዮሐንስ ክፉ ሥራን ይሽራል ተብሎ ይታመናል፤ ‘አብሮ የበላን ቅዱስ ዮሐንስ አይሽረውም’ የሚባለውም ከመልካም ነገር ውጪ ያለው ክፉ ሥራ ሁሉ በበዓሉ ይሻራል ለማለት ነው።

የባህል መድኃኒት አዋቂዎች በሰውነት ላይ እንዲነገቱ የሚያዘጋጇቸው መድኃኒቶች በአዲሱ ዓመትም እንዲታደሱ በዋዜማው ተቀብረው እንዲያድሩና ጠዋት እንዲወጡ ያዛሉ። የጣት ቀለበትና የአንገት ማተብም በዋዜማው ደጃፍ ላይ ቀብረው የሚያሳድሩና የበዓሉ ዕለት አውጥተው የሚያደርጉም አሉ፤ ይህም ቅዱስ ዮሐንስ ያድሳል ተብሎ ስለሚታመን ነው።

መልካም በዓል!
ከ መላኩ ጌታቸው "ክብረ በዓላት - ሃይማኖትና ባህል" መጽሐፍ የተወሰደ

ሐምሌ አቦ! #ክብረ በዓላት - ሃይማኖትና ባህል # መጽሐፍ ከእጅዎ ገባ?!እያነበቡ ምልከታዎንም ያጋሩን! ሐምሌ 5 የሐዋርያቱ የቅዱስ ጴጥሮስና የቅዱስ ጳውሎስ የዕረፍት በዓል ቢሆንም ቀኑ የ...
12/07/2022

ሐምሌ አቦ!
#ክብረ በዓላት - ሃይማኖትና ባህል # መጽሐፍ ከእጅዎ ገባ?!
እያነበቡ ምልከታዎንም ያጋሩን!

ሐምሌ 5 የሐዋርያቱ የቅዱስ ጴጥሮስና የቅዱስ ጳውሎስ የዕረፍት በዓል ቢሆንም ቀኑ የጻድቁ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ወርኃዊ መታሰቢያ በዓል በመሆኑ በአብዛኛው በልማድ ሐምሌ አቦ ተብሎ ታወቃል፤ ጉቡኣን አቦ እየተባለም የጠራል።

ከፍቾዎች ወርኃ ሐምሌን ኹነቱን በማሰብ አውራቲ ይሉታል የሐዋርያት ወር ለማለት ነው።
ዕለቱ ሐዋርያት ለስብከተ ወንጌል ከመሠማራታቸው በፊት መንፈሳዊ ተልዕኳቸው እንዲቀናላቸው የጾሙትን ጾም በመፈጸም ዕጣ ተጣጥለው ሀገረ ስብከታቸውን የተከፋፈሉበትም ነው። ወሩ የሐዋርያት በዓል የሚበዛበት በመሆኑም በየአካባቢው በተለያዩ ቀናት ሐዋርያ እየተባለ ይከበራል።

ሐዋርያት በዚህ ዓለም ሁሉን ትተው ድሆች ስለነበሩ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ይህንን ጾም ጾመው ሲፈጽሙ የፈሰኩት በተልባና በኑግ ነበር፤ በዚህ ምሳሌ ሐዋርያትን አብነት በማድረግ የሚጾመው፥ ጾመ ሐዋርያት በሚፈታበት ቀን፥ በጎንደርና አካባቢው እሪጦ የሚባል እንደ አነባበሮ የሚዘጋጅ እንጀራው ከተጋገረ በኋላ ተልባ ወይም ኑግ ተቀብቶ እንደገና ተደርቦበት ይበስልና ይበላል። ይህን የበላ ልጅ መብረቅ አይመታውም፥ የክረምቱ ብርድም አይጎዳውም ተብሎ ይታመናል።

በደቡብ ጎንደር አካባቢ በዓሉ የጾም መፍቻ በመሆኑ አቅሙ የቻለ በእርድ ያከብረዋል። በኑግ የተዘጋጀ ትኩስ የጤፍ ቂጣም የዕለቱ ዋነኛ ምግብ ነው።

ሐምሌ 5 በተጨማሪም የ72ቱ አርድእት የመታሰቢያ በዓላቸው ነው።

መጽሐፉን ለማግኘት በ+251935 35 09 00 ይደውሉ!

ግሩም መጽሐፍ በእጃችሁ ሊገባ ነው!!ከ ይፍቱስራ ምትኩ
11/06/2022

ግሩም መጽሐፍ በእጃችሁ ሊገባ ነው!!
ከ ይፍቱስራ ምትኩ

አስተሳሰብህን ሳይነካ የማያልፍ - የዓለማችን እጅግ ተነባቢ መፅሐፍ!(በአሳፍ ሃይሉ)1 June 2021ይህ ፅሑፍ "Enjoy Every Sandwitch: Living Each Day As If It ...
07/06/2022

አስተሳሰብህን ሳይነካ የማያልፍ - የዓለማችን እጅግ ተነባቢ መፅሐፍ!
(በአሳፍ ሃይሉ)

1 June 2021

ይህ ፅሑፍ "Enjoy Every Sandwitch: Living Each Day As If It Were Your Last" ከተሰኘውና በመላው ዓለም እጅግ ተነባቢነትን (ተወዳጅነትን) ካተረፈው፣ ከዶክተር Lee Lipsenthal (M.D.) መፅሐፍ ተቀነጫጭቦ የቀረበ ፅሑፍ ነው።

ዶክተር ሊ ሊፕሰንታል የሚጀምረው በጥያቄ ነው፦ "ነገ ትሞታለህ ብትባልስ.. ? ዛሬህን እንዴት ልታድራት ነው የምትመኘው?" በማለት።

ይህን የሚጠይቀው፣ ራሱም ለሞት በቀናት ርቀት ላይ ቆሞ ይመስለኛል። በዚህ ጥያቄ መነሻነት ብዙ ሃሳቦችን አውጠንጥኜያለሁ። የፈለገ፣ ይህን የዶክተር ሊን ህይወትና ተሞክሮ የያዘ መፅሐፍ ያንብብና፣ እንደኔ ተደምሞ ይቅር።

የህክምና ዶ/ር የሆነው ሊ ሊፕሰንታል በጥሩ ቁመናና ብርታት ላይ በሚገኝበት በ52ኛ ዓመቱ ላይ ድንገት አንድ ገጠመኝ ቀሰቀሰው።

አፉ የዶለው የዳቦ እምቡጥ ከጉሮሮው አልወርድ ብሎ መከራውን ያበላዋል። አየር ያጥረዋል። ደረቱ በህመም ይቀሰፋል። እንደምንም ተንደፋድፎ ግን ዋጠውና አየር ለመሳብ በቃ።

ሚስቱ (ኬቲ) ስትመጣ ያጋጠመውን ይነግራታል። አብራው በህክምና ኮሌጅ የተማረች የህክምና ዶክተር ነች። ሁለቱም ሀኪሞች ናቸው። 30 ዓመት በትዳር ኖረዋል። ወንድና ሴት ልጆች አፍርተዋል።

ከታዩት ምልክቶች ህመሙ ምን ሊሆን እንደሚችል፣ ሊ ሊፕሰንታልን ምን እንደገጠመው፣ ሁለቱም ጠርጥረዋል። የፈሩትን ግን ሳይነጋገሩ ተቃቅፈው ያድራሉ።

በማግሥቱ ዶ/ር ሊ ይመረመራል። ካንሰር ተገኘበት። የጉሮሮ ካንሰር። ለካ ሳያውቀው የጨጓራው አሲድ ወደ ጉሮሮው እያሻቀበ ለዓመታት ሲያነደው ኖሯል። እና ካንሰሩ ወደ ሳንባውና ሌሎች አካላቱም ተሰራጭቷል።

መርዳት የማይቻልበት ወቅቱ ላይ ነው ጫን ባለ የዳቦ ትንታ የባነነው። እና በህይወት ለመቆየት ያለህ ዕድል ከዓመት ሁለት-ዓመት ያነሰ ነው የሚል ቁርጥ ያለ (ኮንክሪት) የምርመራ ውጤት ይነገረዋል።

በዚህች ከምርመራው ውጤት እስከ ሞቱ መሐል ባለችው ጊዜ ውስጥ ነው ዶ/ር ሊ ሊብሰንታል ይህን እጅግ ልብ የሚነካ፣ እና ማንንም የሰው ፍጡር በጠንካራ መንፈስ የሚያበረታ፦ "Enjoy Every Sandwitch - Living Each Day As If It Were Your Last" የሚል መፅሐፍ የፃፈው።

የሚያሳዝነው ዶ/ር ሊ መፅሐፉ ከመታተሙ በፊት ቀድሞ (በሴፕቴምበር 20/ 2011 ላይ) ህይወቱ አለፈ።

ከወራቶች በኋላ ዶ/ር ሊ ሊፕሰንታል የሪሰርች ፕሮግራም ዳይሬክተር ሆኖ ለአሰርት ዓመታት የሠራበት የካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ የህክምና ፕሮፌሰር የሆነ የብዙ ዓመት ወዳጁ ዶ/ር ዲን ኦርኒሽ የመፅሐፉን መግቢያና ስንብት ክፍሎች ፅፎለት፣ መፅሐፉ ሊታተምለት በቃ።

ይህ መፅሐፍ ሲታተም፣ በአሜሪካ "ቁጥር-1" best selling መፅሐፍ ከመሆኑ ውጪ፣ በተለያዩ ቋንቋዎች ተተርጉሞ በዓለም ተነባቢ ሆነ።

ይህ መፅሐፍ እና ሌላኛው የዶ/ር ሊ ብዙ ዓመታት ያሳለፈበት የህክምና ዶክተሮች በሽተኞቻቸውን ሲያክሙ ከሚደርስባቸው ጫናና ጭንቀት ነፃ ሆነው የሚኖሩበትን የህይወት ልምምድ፣ መንገድና ተሞክሮ የሚያካፍለው መፅሐፉ፣ በአሁኑ ሰዓት በመላው አሜሪካ ለresident ሀኪሞች ሁሉ እንደ ኮርስ ሲለበስ ይሰጣሉ።

ይህች ቁመቷ አነስተኛ ሆና 190 ገፆች ገደማ የያዘች "Enjoy Every Sandwitch - Living Each Day As If It Were Your Last" መፅሐፍ የምታስጨብጣቸው የህይወት ቁምነገሮች ብዙ ናቸው።

የህይወት "ስኬት" (a success in life) ማለት፣ በሙያ ወይም በገንዘብ ወይም በሌላ በዓለም በታወቀ መለኪያ የምትቀዳጀው፣ ቁርጡ የታወቀ ነገር ሳይሆን፣ ራስህ የምትወስነው ደስተኛ ህይወትን መምራት የመቻል ውስጣዊ የእርካታ ስሜት ነው ይላል ዶ/ር ሊ።

ኖረህ ኖረህ የሞትህ ቀን ላይ ስትደርስ፣ "አሁን ብሞትም ዝግጁ ነኝ"፣ "ደስተኛ ነኝ"፣ ብለህ ከፀፀትና ትካዜ ነፃ ሆነህ መገኘት የምትችልበት ህይወት ካለህ፣ አንተ በትክክል ህይወትን ሙሉዋን ኖረሀታል ማለት ነው ይለናል።

በስተመጨረሻ ሞትህ ፊትህ ተደቅኖ ሲቆም እንዳይቆጭህ፣ የምትማረርበትን የህይወት መስክ ጊዜ ሳታባክን ቀይረው ይላል ዶ/ር ሊ።

በህይወት ስትጓዝ "ሪስክ" ውሰድ፣ ለውጥን አትፍራ፣ ለውጥ የሚያመጣልህ ነገር ወይም የሚወስድህ ሥፍራ ምን እንደሆነ ባታውቀው እንኳ፣ ካማረረህ ህይወት ፈቅ ለማለት የምትደፍር የህይወት ጀግና ሁን ይላል።

የህይወትህ ጀንበር ሳለች አፍቅር። ከሰው ተግባባ። ከማህበረ- ሰብህ ተቀላቀል። ለሰዎች ምስጋና ይኑርህ። ለህይወት ምስጋና ይኑርህ። ለሰዎች የምታስተርፈው ርህራሄ አትጣ። ይላል ዶ/ር ሊ።

መንፈሳዊ እሴቶች፣ በህይወትህ ሳለህ ቋሚ ልምዶችህ እንዲሆኑ መለማመድ፣ ንዴትና ቁጣዎችህን ወደ ፈጠራና መልካም ነገሮች መለወጥ፣ ለሰው ህይወት እጅግ ቁልፍ ነገሮች መሆናቸውን ከራሱ ጥሩም መጥፎም የህይወት ምሣሌዎች እየጠቀሰ ነው የሚያስረዳው።

በሞት ፊት በቀረብኩ ሰዓት፣ ልቀይራቸው የማልችላቸውን ነገሮች እያሰብኩ ተረዳሁ፣ ሰዎችን በመጥላት ያሳለፍኳቸው ጊዜዎች ደስታን ለመፍጠር ተለክታ ከተሰጠችኝ ህይወት፣ የቱን ያህል ታላቅ ብክነት እንደነበረ በመጨረሻው ሰዓት ተረዳሁ፣ ይለናል።

ገና ለገና "ብዙ ዘመኔን ፈጀሁበት" "ብዙ ነገሬን አባከንኩበት" ብለህ የተሳሳተ መሆኑን የምታውቀውን የህይወት መንገድ ሙጭጭ ብለህ ሞት ፊት እንዳትቀርብ፣ እና "አንድ ቀን ደስ ያለኝን ህይወት መርጬ በኖርኩ"፣ "አንድ ቀን ህሊናዬን አስደስቼ ቢሆንስ ኖሮ"፣ ብለህ እንዳትፀፀት አድርገህ ኑር፣ የሚለው ምክር፣ ደግሞ ደጋግሞ ፅፎልን የምናገኘው ምክር ነው።

ዶ/ር ሊ ይቅርታ እጅግ አስፈላጊ ነው ይላል። Forgiveness! The easiest amd kindest gift you have in your hand is the ability to forgive! Forgive, but do not forget! ("ይቅር በል፣ ግን አትርሳ!" - ለሌላ ጊዜ ትምህርት እንዲሆንህ።

"ከታጠርክበት ሳጥን ደሞ በፍጥነት ውጣ!" ይላል። Get outside of the box! Now! የአስተሳሰብ ሳጥን ነው? ወጣ በልና ተመልከተው። የሙያ ሳጥን ነው? ወጣ በል። የኑሮ ሳጥን ነው? ከእሱም ውጣ። የዕድሜ ሳጥን? ውጣ ከእርሱም።

ከተከረቸምክበት የህይወት ሳጥን ተሳክቶልህ መውጣት እንኳ ሳትችል ብትቀር፣ ቢያንስ ቢያንስ፣ ከሳጥኑ ለመውጣት የቻልከውን ከመሞከር አትቦዝን። ሳጥኑን ሳትቧጥጥ ኖረህ፣ በመጨረሻ፣ አይቀሬው የሞት ሳጥን ፊትህ ሲቀርብ ማየት - እጅግ አስከፊው የህይወት መሪር ሽንፈት ነው ይላል።

ዶ/ር ሊ ሊፕሰንታል ከሚያነሳቸው ቁምነገሮች መካከል እጅግ የመሰጡኝ ሁለት ሳይንሳዊ ግኝቶች አሉ። (ራሴም በአጋጣሚ በሌላ ሁለት መፅሐፎች ስለእነዚሁ ቁምነገሮች እያነበብኩ በመሆኑም ጭምር ገርመውኛል)።

አንደኛው "ኒውሮፕላስቲሲቲ" (Neuroplasticity) ስለተሰኘው የአንጎላችን ራሱን የመቀየር ችሎታ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደሞ ስለ "ብሬይን ዌቭስ" (Brain waves) ወይም የአዕምሯችን እንደ ኔትወርክ ከሰውነታችን ወጥተው ከሌሎች ፍጡራን ጋር ስለሚያገናኙን ተሻጋሪ invisible ሞገዶች የሚያስረዳው ነው።

ኒውሮፕላስቲሲቲ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግኝቱ ከታወቀና አግኚውን ኒውሮሳይንቲስት ኤሪክ ካንደልን የፊዚዮሎጂ ኖቤልም ካሸለመ በኋላ፣ ብዙ አስደናቂ ነገሮቹ ምርምር እየተደረገበት ያለ የሰው ልጅ አስደናቂ ፀጋ ነው። ባጭሩ የህይወት ተሞክሯችንና ሀሳባችን አንጎላችንን ይሞርደዋል የሚል ግኝት ነው።

ለምሳሌ በጣቶቻችን የሙዚቃ መሣሪያ መጫወትን ስንለማመድ፣ የጭንቅላታችን አካላዊ እንቅስቃሴን የሚያቀላጥፉ ጥቃቅን ህዋሶች (motor neurons) በብዛት የሚተላለፉበት የአንጎል ክፍል - በችሎታውና አቅሙ - ከሌላው የሙዚቃ መሣሪያውን ከማይጫወተው ሰው ይልቅ - ከፍ ብሎ ይገኛል።

ዓይነ ሥውራን ለምሳሌ አያዩም። ስለዚህ ሰውነታችን ብርሃናማ ምስሎችን ለመከሰት የሚጠቀምበት visual cortex (ቪዥዋል ኮርቴክስ) የተባለው የአንጎላቸው ክፍል በድን መሆን ነበረበት።

ሆኖም ዓይነ ስውራኑ ለምሳሌ በዓይኖቻቸው ምትክ በብሬይል ለመፃፍ ጣቶቻቸውን ይጠቀማሉ፣ በዓይናቸው ፋንታ የመዳሰስና የመስማት የስሜት ህዋሶቻቸውን ይጠቀማሉ።

እና በሚገርም ሁኔታ የዓይነ ሥውራን አንጎል ይህን እውነታ ተረድቶ፣ ዓይነ ሥውራኑ ሲፅፉ ወይም ሲሰሙ፣ ለወትሮ ለእይታ የሚያገለግለው "ቪዥዋል ኮርቴክሳቸውም" አብሮ በተግባሩ ላይ ይሰማራል።

ይህ ማለት ምን ማለት ነው? ዓይነ-ሥውራኑ ሲሰሙ የሚሰሙት ድምፅ ብቻ አይደለም ማለት ነው። የሚሰሙት ድምፅ፣ እና በድምፁ የሚተላለፈው ሃሳብ፣ በአንጎላቸው እንደ ምስል ሆኖ ይከሰትላቸዋል ማለት ነው።

ዓይነ-ሥውራኑ ሲያነቡ፣ በጣቶቻቸው ፊደሎቹን ሲነካኩ፣ ልክ እኛ በዓይናችን ምስል ስናይ visual cortexሳችን ያን ምስል በአንጎላችን ለመከሰት በሚሠራበት ተመሣሣይ አኳኋን፣ የቪዥዋል ኮርቴክሱ ህዋሶች፣ በዳሰሳና በድምፆች መነሻነት፣ በዓይነስውራኑ አንጎል ምስሎችን ለመከሰት ከፍተኛ እንቅስቃሴዎችን ሲያደርጉ ተስተውሏል።

በጭንቅላታቸው የፊደላቱና የያዟቸው ሃሳቦች ምስሎች፣ ልክ እኛ በዓይን አይተን በዕዝነ ህሊናችን በሚቀረፅበት መልኩ፣ ይቀረፁላቸዋል ማለት ነው።

በነገራችን ላይ ይህ የአዕምሯችን ተሞክሯችንን የመከተል ነገር፣ ለዓይነስውራን ብቻ የተሰጠ ፀጋ አይደለም።

ለምሳሌ በህይወታቸው በብዛት አንድን የሙዚቃ መሣሪያ የሚጫወቱ ጊታሪስቶች፣ ፒያኒስቶች፣ ወዘተ፣ በእጆቻቸው የሚጫኗቸውን ክሮችና ቁልፎች በዓይኖቻቸው መመልከት ሳያስፈልጋቸው፣ በቀጥታ በጆሯቸው የሚተላለፈውን የሙዚቃ ክር ድምፅ በመስማት ብቻ፣ አሊያም በጣቶቻቸው በመጫን ብቻ፣ አጠቃላይ የሙዚቃ መሣሪያው፣ ዓይኖቻቸውን ጨፍነውም፣ ወለል ብለው ይታዩአቸዋል።

ይህ የአንጎላችን ተዓምር ነው። የአንጎል ምስል መከሰቻ visual cortex በዓይን ውስጥ የሆነ ምስል ዕይታ ውስጥ ሲገባለት active የሚሆን የአንጎል ክፍል ነበር። ነገር ግን ይህንን አሠራሩን ለውጦ፣ ተደጋጋሚው ድምፅ ሲመጣለት፣ ወይም የለመዳት ክር ስትነካለት፣ ምስሎችን በማይታይ ካሜራ እየቀረፀ ለጭንቅላታችን አከታትሎ መላክ ይጀምራል ማለት ነው።

ስለዚህ አንጎል ውጫዊ አካላዊ ተሞክሯችንን አይቶና መዝኖ፣ ሥራ ለሚበዛባቸው ኒውሮኖች ተጨማሪ አቅም ያላብሳቸዋል ማለት ነው። እና ባጭሩ ይህን የአንጎላችንን - እኛ ራሳችንን በህይወታችን በብዛት ባሠማራንበት አቅጣጫ ራሱን የመቀየርና አቅማችንን የማበልፀግ ኃይሉን ነው "ኒውሮፕላስቲሲቲ" የምንለው።

ይህን የneuroplasticity concept ዶ/ር ሊ ወደ መልካም ሀሳቦች ያሻግረዋል። ሁሌ የነገሮች ጉድለትና ጨለማ ጎን ላይ አተኩረን እንከን የምናነፈንፍ ሰዎች ከሆንን፣ አንጎላችን ያንን "negative energy" (አሉታዊ ነገሮችን የማነፍነፍ አቅማችንን) ነው የሚያጠናክርልን ወይም reinforce የሚያደርግልን!

ብዙ ጊዜ አዕምሯችንን ለማመስገንና ቀና ቀና ነገሮችን ለማነፍነፍ ከተጠቀምንበት ደግሞ፣ አንጎላችን ጨምሮ ጨማምሮ "activate" የሚያደርግልን፣ ያንን ቀና ነገርን የማነፍነፍ አቅማችንን ነው።

ስለሆነም፣ ሆነ ብለን ጥሩ ጥሩ ነገሮችን ለማሰብ በመምረጥ፣ አንጎላችንን ወደ ጥሩ አሳቢ ማሽንነት ለመቀየር እንችላለን! አለበለዚያ ደሞ በየእርምጃችን ጉድለትንና እንከንን ለማሰብ በመምረጥ፣ አንጎላችንን ወደ ፀጉር-ሰንጣቂ ማሽንነት መቀየር እንችላለን! ምርጫው በእጃችን ነው ይለናል።

(ዶ/ር ሊ ይህን ሲል በገዛ እጄ ወደ ፀጉር-ሰንጣቂ ማሽንነት የለወጥኩት የገዛ ራሴ ጭንቅላት አብዝቶ አሳዘነኝ!😁😄)።

የኒዩሮፕላስቲሲቲ ጉዳይ ጥልቅና ሰፊ ነው። በዚህ ብቻ አያበቃም። በሂደት "ኒውሮጂንስ" (neurogenes )የሚባሉትም የጀነቲክ ኮዶች ይፈጠሩና አንጎላችንን ያለማመድነውን ባህርያችንን በዲኤንኤያችን ላይ አትመው ለቀጣዩ ትውልድ (ለምንወልደውም ልጅና የልጅ ልጅ ሁሉ) ያን የባህርይ ቅንጣት ያስተላልፉታል።

(ሀበሻ "የማን ዘር ጎመን ዘር" የሚለው ነገር ለካ የሆነ ሳይንሳዊ ይዘት እንደነበረው መጠርጠር የጀመርኩት አሁን ነው😁😄። (ወይኔ ልጄ!!!😁😄🤔😭)

ይህን ጉዳይ ሌላ ጊዜ ስለምመለስበት ሳልወድ እዚህ ላይ ላቁመውና ወደ ዶ/ር ሊ ሁለተኛው ሳይንሳዊ እውነታ ልሻገር። ስለ ብሬይን-ዌቪንግ (Brain waving)።

ይሄ ሁለተኛው ሳይንሳዊ ምርምር ደሞ የተሠራው የሁለት ጎን ለጎን ተቀራርበው የሚቀመጡ ሰዎችን የልብ ምት በኢሲጂ - (electro-cardiography) ምርመራ በመለካት እና የእነዚህኑ ሰዎች የአንጎል ኒውራል ሞገዶች በኢኢጂ (electro-encephalogram) ምርመራ በመለካት ነው።

ለምሣሌ፦ የሆነ ሰው ተቀምጦ የልብ ምቱና የአንጎል ሞገዱ መጠን እየተለካ ነው፤ በመሐል ሌላ ሰው አጠገቡ እንዲቀመጥ ይደረጋል፤ እና የሁለቱንም የልብ ምቶችና፣ የአንጎል ኤሌክትሪካዊ ሞገዶች መለካቱ ይቀጥላል።

በሚገርም ሁኔታ፣ ከጥቂት ሰከንዶች በኋላ የሁለቱ አጠገብ ላጠገብ የተቀመጡ ሰዎች ልቦችና ሞገዶች፣ በየራሳቸው ወጣ ገባ ሪትም መምታታቸውን አቁመው፣ ራሳቸውን በማመሳሰል፣ እንደ ተለማመደ ሰልፈኛ፣ የሁለቱም ልብም አንጎልም አንድ አይነት ታምቡራዊ ሪትም፣ አንድ ዓይነት የfrequency ሞገድ ሲደልቁ ይገኛሉ!

የምርምሩ ውጤት ልባችንና አንጎላችን እኛ የማናውቀው ከሰውነታችን ውጪ ያለን የሌላ ሰው ልብና አዕምሮ የሚያነብበትና ራሱን የሚያስማማበት ተፈጥሯዊ ስጦታ እንዳለው አረጋግጧል።

ዶክተር ሊ ሮዘንታል ይህን አስደናቂ ግኝት፣ በsocial context ቀይሮ ሲተረጉመው ምን ይላል? ይህ ማለት፣ ከሰው ጋር ከመጣላት ይልቅ መግባባት፣ በተመሣሣይ የግንኙነት ፍሪኩዌንሲ ላይ መገኘት፣ ልብ ለልብ መናበብ፣ በተመሣሣይ ደረጃ ተግባብቶና ተናብቦ መገኘት፣ የሰው ልጅ ተፈጥሯዊው ሥሪት ነው ማለት ነው።

ከሰው ጋር ለመግባባት አንጎልህ ራሱ ሳትጠይቀው ያግዝሀል፣ ከሰው ጋር ለመጣላትና ለመናቆር ግን ጭንቅላትህን በግድ መጠምዘዝ ይጠበቅብሀል።

ዶ/ር ሊ ተፈጥሮ አንድ ፍጡር ከመሠሉ ሌላው ፍጡር ጋር በወገንነት የሚግባባበትና የሚቆራኝበት አንዳች አስማታዊ አካላዊና አዕምሯዊ ብቃት ገጥማልን ነው በምድር ላይ ያሰማራችን ማለት ነው።

Nature downloaded in everyone of us this amazing inter-species syncronization software and hardware by default! ተፈጥሮ የኢንተር ስፒሽስ ሲንክሮናይዜሽን ሶፍትዌርና ሀርድዌር ጭናልናለች።

መልካሙን ተፈጥሮህን፣ ወይም ጠማማውን አመልህን የመጠቀሙ ምርጫ ያንተው ነው ይልሀል ዶ/ር ሊ።

ከሰው ጋር ለመግባባት በምታደርገው ጥረት፣ የተገጠመልህ ሰዋዊ ተፈጥሮህ ያግዝሃል! ከሰው ጋር ለመጣላትና ለመበላላት ግን ከተፈጥሮህ ጋር ትግል ገጥመህ ነው የምታከናውነው! ሠላምህ የእግዜርህ ሥጦታ ነው። ጠብህ ግን ራስህ ያመጣኸው ቃየላዊ ዝንባሌህ ነው። እና brother፦ "ወደ ተፈጥሮህ ተመለስ"!

በመጨረሻ ዶ/ር ሊ የሚናገራት የሰው ልጅ ተፈጥሮን የምትገልፅ አንዲት scientific fact እጅግ መስጣኛለችና እሷን አንስቼ ልሰናበት።

ዶ/ር ሊ የሚነግረን ሌላው ግኝት ሰዎች እንዲወዱህ ውደድ፣ እንዲያደንቁህ አድንቅ፣ እንዲያመሰግኑህ አመስግን፣ እንዲያፈቅሩህ አፍቅር፣ የሚለው ተፈጥሯዊ መርህ ነው።

ይህ ደግሞ የተጠናው ሰዎች አንድን የተቆጣ ሰው (ወይም እንስሳ ለምሳሌ አዞ)፣ እና አንድን ለስላሳ ሰው (ወይም እንስሳ ለምሳሌ ለማዳ እርግብ) እርስበርስ አንዳቸው ሌላኛቸውን የሚቀርቡበትን አካላዊ ርቀትና መጠጋጋት (electro-magnetic fieldዳቸውን) በመለካት ነው።

ለምሳሌ በቀላሉ በሆነ ርቀት አዞ ቢያስቀምጡልህ በምን ያህል ርቀት ትጠጋዋለህ? አፉ የታሠረ ቢሆን ራሱ አዞውን የምትቀርበው በሆነ ርቀት አፈግፍገህ ነው።

ለማዳ የቤት እርግብ ወይ ድክ ድክ የምትል ህፃን ቢያቀርቡልህስ? አሁን ደሞ እግርህ ራሱ ሳትወድ "ተጠጋ ተጠጋ" ይልሀል። አካልህ ራሱ አንተ ሳታዘው ወደ ፀባየ-ሸጋው ይመራሀል፣ ይስብሃል። ከፀባየ ቁጡው ደሞ ያርቅሀል።

ስለዚህ ሰዎች የአንተን ባህርይ በተወሰነ ማግኔቲክ ፊልድ ርቀት ላይ ሆነው በመረዳት፣ በተላበስከውና ባሰብከው ልክ ሊቀርቡህም፣ ሊሸሹህም እንደሚችሉ ዕወቅ! - ይላል ዶክተር ሊ።

ሰዎች እንዲቀርቡህ ከፈለግክ፣ መጀመሪያ አንተ "አቅራቢ ባህርይ" አሳይ፣ እንዲሸሹህም ከፈለግክ "ጨጎጊት" ሆነህ መገኘት ያንተ ምርጫ ነው። "እሹ፣ እንዳሰባችሁት እንደዚያው ታገኛላችሁ!" እንዲል ቅዱስ መፅሐፉ።

ባጠቃላይ ዶ/ር ሊ ከሞት ፊት በደስታና በእርጋታ ቆሞ በዓመታት ምርምሮቹ፣ የህይወት ተሞክሮውና በመጨረሻዎቹ የህይወቱ መዝጊያ ቅጥሮች ላይ ቆሞ፣ ለሰው ልጆች ብናገር በእጅጉ ያተርፉበታል፣ ከመቆጨት ይድናሉ፣ ብሎ ያሰበውን ሁሉ የሰውን ልጅ በሚያፈቅር ርህራሄን በተሞላ ልብ አካፍሎናል።

ይህ አስደናቂ የህክምና ሳይንስ ተመራማሪና ስፔሻሊስት ሃኪም። መንፈሳዊ ፅሞናዎችና ዕለታዊ meditation practices በሰውነታችንና አንጎላችን ላይ ስለሚያመጡት አስደናቂ ውጤት በመመራመር ለአሰርት ዓመታት የተጠጋ ምርምሮችንንና ልምምዶችን ሲያከናውን የቆየው፣ ዶ/ር ሊ ሊፕሰንታል፣ ሰው ነውና፣ ባላሰበው ሰዓት፣ ብዙ ማበርከት በሚችልበት፣ ብዙ ነገሮችን በተረዳበት ዕድሜው፣ ይህቺን ዓለም በደስታ ተሰናበተ።

ህይወትን በሳንድዊች በመመሰል ቀስ እያልን እንድናጣጥማት፣ እንደ አንድ ሃኪም ብቻ ሆኖ ሳይሆን፣ ገና ኮሌጅ የገቡ፣ እና መመረቃቸውን የማያየው የሁለት ወንድና ሴት ልጆች አባት ሆኖ፣ እንደ መልካም አባት፣ ለሰው ልጆች ሁሉ ይጠቅማል ያለውን፣ የተረዳውን፣ ያየውን በመልካም ልብ አካፍሎናል።

በመግቢያዬ እንዳልኩት፣ ዶክተር ሊ ሊፕሰንታል የልጁን የኮሌጅ ምርቃት ብቻ ሳይሆን፣ የመፅሐፉንም ምርቃት ሳያይ ነው አይቀሬውን ሞት ያስተናገደው። ከሞላ ጎደል፣ ያስተላለፈልን "የመልካም አባት ኑዛዜ" የሚመስሉ አስገራሚ የህይወት ምክሮች እኚህ ናቸው።

ህይወትን በፍቅር፣ በመቀራረብ፣ በመመሰጋገን፣ በይቅርታ፣ በእርጋታና በርህራሄ ብንኖራትስ? - አንድዬ ይርዳን።

የዶክተሩን ነፍስ ፈጣሪ በሠላም ያሳርፍለት።

ፈጣሪ ኢትዮጵያችንን በፍቅር ይባርክ!

መልካም ጊዜ።

ይሄ ትውልድ እና ዘመን እንዴት በአዳም ተረታ? 1. አዝማሪው ባህሩ ቀኜ፡፡ "በሽተኛው በዛ መድኃኒት አነሠው" የሚል ስንኝ አላቸው፡፡ የኔ ዘመን እና ትውልድን ለመግለፅ ምቹ ነው የባህል አር...
25/05/2022

ይሄ ትውልድ እና ዘመን እንዴት በአዳም ተረታ?

1. አዝማሪው ባህሩ ቀኜ፡፡ "በሽተኛው በዛ መድኃኒት አነሠው" የሚል ስንኝ አላቸው፡፡
የኔ ዘመን እና ትውልድን ለመግለፅ ምቹ ነው የባህል አርበኛው ንግግር፡፡

አዳም ረታ ዘመኑ እና ትውልዱ "በእንከን የተሞላ በመኾኑ" ሊተወን አልወደደም፡፡ እንጀራ የተባለ ትዕምርት አነሳ ፤ እንጀራ የተባለ ትርክት ተዋሰ ከድርብ ፤ ድርብርብ ኑሮአችን፡፡ (Surplus life)
እንጀራንም በአይኑ ÷ በክብነቱ ÷ በየትየለሌ የጤፍ እድሜ እና ስልጣኔ ውስጥ (Geez and teff civilization) የዚህ ዘመን "መድኃኒት" ሊያደርገው ወኔ ሰነቀ፡፡ (Cultural elite literary courage and critical internal journey ነው፡፡

እንጀራ አንድምታ hegemonic understanding ውስጥ አልነበረም፡፡ የተጣጣለ ፤ የተነወረ የኑረታችን መንገድ ነበር፡፡ ወይ አለማወቅ፡፡

አዳም ታዲያ ሊቀ ሊቃውንት ነውና "እንጀራን ከተነወረበት አነሳ ፤ ጤፍን ደቃቅነቷን አከበራት" የእንጀራውን ዓይን ማያ አደረገው፡፡ ባለ ብዙ እይታ ሠራበት፡፡ ወንድ እንጀራ ጋጋሪ ሆነልን፡፡

ዘመኑ እና ትውልዱ በ Meta narrative አብዷል፡፡ በ hegemonic notion ከስሯል፡፡
አዳም ግን ሌላ ነው፡፡ እንጀራ በአገራዊ ውክልናችን ውስጥ ዳረኛ ነው፡፡ አገሩ እና ህዝቡ የገናናው እሳቦት ብቻ ሳይሆን ÷ የ non state actor ነው አለ፡፡ አገር እና ባለ አገር የሁሉም ውክልናዎች Space politics ነው ብሎ በረታ፡፡ ኢትዮጵያንም ከአገራዊ ብሔርተኞች እና ከንዑስ ብሔርተኞች አታሞ ሊያድን እና ከ linear notion አፋታ፡፡ እንጀራ መታረቂያችን ፤ ነገን መስሪያ ትዕምርት ፤ ምሳሌያችን ነው አለ፡፡ Centripetalism ሊሠራበት ቀደመ፡፡
ይሄ ትውልድ ዘረኛ ፤ ጦረኛ ፤ ብሔርተኛ ኾኖ አዳም እወዳለው ሲል፡፡ አዳም የወል ሲኾን እደነግጣለሁ፡፡ እኛ የእሱን አዲስ ተረክ ፤ የእሱን አይነ ኅሊና እንደተጋራን አላየሁም እና ÷

2. እንጀራ ÷ የጋራ ትዝታችን የተሰራበት ፤ የተጋገረበት አውድ ነው፡፡ የጋራ ትዝታ ያለው አገር እና ትውልድ ደግሞ "ሰው አለ ተብሎ ይፈታል ወይ ትዳር" አይከናወንበትም ነበር፡፡

ፅድቁን ፤ እንጀራውን ጠብቆ ያሳይ ነበር፡፡ አዳም እንጀራን ለትናንት ትዝታ ብቻ ሳይሆን ፤ ለነገ ትዝታም ማዘመኛ ዘይቤው ነው፡፡ ይህ ዘመን እና ትውልድ የራሱ እውቀትን የማያውቅ ÷ የአለሙን ጥበብ ያልተረዳ ነው፡፡ በራሱ ላይ ያመፅ ፤ ምን መሆን እንደሚፈልግ በአግባቡ ያልተረዳ ነው፡፡Lack of epistemic autonomy አጋጥሞታል፡፡ በዚህም ምክንያት ከእንጀራ ተምኔት ይልቅ ፤ በሌላኛው ዓለም አለባበስ ÷ ምሳሌ እና ህልም ሰክሯል፡፡ የበላበትን ወጪት ሰባሪ ኹናል፡፡ (Political destitution and cognitive oppression) እያሰቃየው ነው፡፡

እንደ አዳም ረታ እንጀራውን ተውሶ እውቀቱን አልፈከረም፡፡ ከአዳም የእንጀራ ፍልስፍና ውስጥ የእንሰት ÷ የገዳ ÷ የሽምግልና ÷ የእቁብ ÷ የቅዳሴ/የአዛን/ ትዕምርቶችን አላስፋፋም፡፡ ወደ Dead end እየተጋዘ ነው፡፡

እንደምን ታዲያ የአዳም ረታ ደቂቅ ነኝ ሊል ደፈረ ትውልዱ እና ዘመኑ?

3. ህፅናዊነትን እና አዳም አገራችን እና ሰው የነጠላ አስተሳሰብ ÷ የባለ አንድ መልክ የዝማሬ ፤ የቋንቋ ውጤት እንዳልሆኑ ያምናሉ፡፡ አገራችን እና ዓለማችን በተለያዩ ፅንሠ አሳቦች ÷ የዓለም አተያይ አረዳዶች እንደፀኑ ያምናሉ፡፡ በአባቶቻችን እና እናቶቻችን የቀደመ እውቀት አነጋገር "አገራችን የአንድምታ ውጤት ነች ይላሉ፡፡" Fusions of horizons ይሉታል፡፡
ህፅናዊነት Complex of web connection ነው፡፡ አዳምም አንድንም ታሪክ ብቻውን አድርጎ አያውቅም፡፡ ዘመድ ፤ አዝማድ ፈልጎለታል፡፡ መነሻውን ÷ መጋዣውን እና ማረፊያውን ይሰፋዋል፡፡ ከነጠላ ትርጉም ይልቅ ፤ የምስጥር ትርጉም ውስጥ ያጠምቀዋል፡፡ በሚሼል ፉኮ አነጋገር Deform የኾነውን ተረክ ወደ መዳኛው ይስበዋል፡፡ ያም ህፅናዊነት ነው፡፡ አይነተ ብዙኃነት የኾነ እውቀት ፤ ጥበብ እና መላ እንደኾነ ያሳየናል፡፡ (Emancipator common good)
ይሄ ዘመን ታዲያ እንዴት አዳም በሁለንተናዊነት ውስጥ እንኑር ሲል እንዴት ብቻ ለብቻ ነው የምንቆም እያለ እንዴት ለአዳም ረታ እልልታ አደረገ?

4. አዳም ለቃል ትልቅ ዋጋ አለው፡፡ አባቶቻችን ፤ እናቶቻችን ልሳን ይሉታል፡፡ የአዳም ረታ ልሳን ÷ ምናብ ጥልቅ ፍከራ አለው፡፡ ትርክትህን ÷ ትልምህን ÷ ኑረት ÷ ፍካሬ ÷ ፍልሱፍህን ያተመበት ነው፡፡ አዳም በጣም ቀላል ፤ ገላጭ በኾነ መንገዶች ቃላቱን ይሰራቸዋል፡፡ የቃል ፈጣሪ ነው፡፡ የእኔ እና የአንተን የተበላሸ አለም ለመስራት ቃል ይወልዳል፡፡ ይተቻል ፤ ይወያያል ፤ ይደማመጣል አዳም፡፡ (Trans critique and dialogical critical dialogue)
ዘመኑ እንደምታውቀው ነው፡፡
የስድብ ፤ የጥላቻ ፤ የልዩነት ፤ ነገን የመስበር ቃላቶች የሚመረቱበት ነው፡፡ መወያየት መልካም የተባለውን ወርቅ አሳብ ቀብሮታል፡፡ ቀልብ ÷ ልብ እና ኅሊና የፈረሱበት ናቸው፡፡ (one directional narrative)
እና ይህ ትውልድ አዳምን እወዳለሁ ሲል ንፍጡን እየቀባው ይሆን?
5. ፈላስፋው ዘርአያዕቆብ እንዲህ ይላል "we can’t reach truth through the doctrine of men, for all men are liars"
አገሩ ÷ የወንድ ውልድ ነው፡፡ መንገዱ ፤ ብገሩ ፤ ተስፋችን ፤ ምሬታችን በወንድ አዕምሮ የተበለተ ነው፡፡ የማኅበረሰባችን ማህፀን የኾኑት ሴቶችን እርባና ፤ ውለታን ይረሳል፡፡ ያጣጥላል በመዋቅራዊ አወቃቀሩ፡፡
አዳም ውሸታም ከተባሉት ፤ አጭቤዎች ከተሰኙት ወንዶች ይልቅ በሴቶች አማካኝነት ፍካሬውን ፤ ቁስሉን ፤ ሙክረቱን (ኤክስፐርመንቱን) ያጦዛል፡፡ ማኅሌት ÷ እቴሜቴ ሎሚ ሽታ ÷ እንጀራ የሴትነት ተረክ ናቸው፡፡ ማሠቢያ ፤ ማውጠንጠኛዎቹ ናቸው፡፡
የወንዶቹ ስርአት አገሩን እና ትውልዱን ምን እንዳሳጣው ካወቅን፡፡ እስከ መቼ የሴቶቻችንን የገደል እና የአርነት መንገድን ሳንጠቀም እንቆይ የሚል ይመስለኛል አዳም ረታ፡፡ በሴት ዓይነ ኅሊና ÷ በሴት ዝክረ ልቡና ÷ በሴት ማኅፀን አዲስ ኢትዮጵያ ሊወልድ የሚውተረተር ይመስለኛል፡፡
አንተ ወንድ ትውልድ ሆይ ፤ እስከ መቼ ሴት ሳትሆን ትቀራለህ?
ሴት አትሆንም ወይ ወንድነትህን ይዘህ እንደሚለን አምናለሁ፡፡
Rejection of monism, point’s horizon to the silence and blind spot of tradition

6. ሊቀሊቃውንቱ ማዕምር መናዕሰናይ ስለ ኢትዮጵያ እንዲህ ይላሉ "The incompleteness of ethiopia doesn’t lead to dead end, on the contrary it drives Ethiopian reality it is."
አዳም ረታም ኢትዮጵያ ጉድፍ እንዳለባት ያምናል፡፡ ጉድፍ ስላለባት ግን ሊተዋት አልወደደም፡፡ ቀጣዩን ምዕራፍ አብረን እናብጀው ብሎ ለሁላችን ነው ጥሪ የሚያደርገው፡፡ ይህንን ለመስራትም ምናብ እና ሁለንተናዊ ውክልና እና እውቀትን መሳሪያዎቹ ያደረገው፡፡ (Political imagination for the future)
በታሪኮቹ ውስጥ ማለቅ የለም የሚለን ÷ አንባቢን እንዲያስብ ፤ እንዲያሰላስል ፤ ከትርክቶቹ ጋር እንዲነጋገር ሲያደርገው የነገን ምዕራፍ የእኔ ብቻ ሳይሆን ፤ የአንተም ነው በማለት ነው፡፡
የዛሬይቱ እና የነገይቱን ኢትዮጵያ ሊሰራ ሁላችንም አለንበትን በ inter textually ህብረ ቃል ያጣብቀናል ፤ እንዳንለያይ አድርጎ፡፡ ይሄ ነው ኹላችንንም አርነት የሚያወጣን ይላል አዳም በቴክኒኩ፡፡

የኔ ትውልድ ግን ስታፈርስ ነው ያየውህ፤ የኔ ዘመን ግን ስትክድ ነው ያስተዋልኩህ፡፡

የኔ ዘመን እና የኔ ትውልድ ሆይ አዳምን ከወደድክ ፤ ደቂቀ አዳም ነኝ ካልህ ፤
ምናቡን ተዋስ ÷ ሁለንተናዊ ትርክቱን አፅናለት ÷ የጋራ የወል ትዝታ እና ፊውቸርህን አስተካክል፡፡
እንከንን ወደ ወርቅነት ቀይር፡፡

ሰው እንኹን፡፡ (Tran’s individual panoptic gaze)

Credit - Habtu Girma

"ክብረ በዓላት - ሃይማኖትና ባህል" መጽሐፍከግንቦት 16 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ በአንባቢዎቹ እጅ መግባት ይጀምራል።መጽሐፉ በዓመት ውስጥ በተለያዩ ጊዜያት የምናከብራቸውን በዓላት፥ ትውፊታ...
23/05/2022

"ክብረ በዓላት - ሃይማኖትና ባህል" መጽሐፍ
ከግንቦት 16 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ በአንባቢዎቹ እጅ መግባት ይጀምራል።

መጽሐፉ በዓመት ውስጥ በተለያዩ ጊዜያት የምናከብራቸውን በዓላት፥ ትውፊታዊ ይዘትና አካባቢያዊ መልክ እያስቃኘ ከሃይማኖታዊ መሠረታቸው ጋር አያይዞ የሚያስረዳ ጥናታዊ መረጃዎችን የያዘ ነው።

መጽሐፉን በ 0935 35 09 00 ደውለው ይዘዙን!

ከጋኒ ምን እንማር? («ለወሬ የለው ፍሬ»!) (የተፃፈ በአሳፍ ሀይሉ)FIXING FAILED STATES – A FRAMEWORK FOR REBUILDING A FRACTURED WORLDወሬ ፍሬ የለው...
15/05/2022

ከጋኒ ምን እንማር? («ለወሬ የለው ፍሬ»!)
(የተፃፈ በአሳፍ ሀይሉ)

FIXING FAILED STATES – A FRAMEWORK FOR REBUILDING A FRACTURED WORLD

ወሬ ፍሬ የለውም - ማለት ወሬ እርባና-ቢስ ነው፣ ፍሬ አያፈራም - ማለት ነው? ወይስ ወሬን ዘርተህ የምታገኘው ነገር አይደለም፣ ከመሬት አይታፈስም፣ የራሱ ወግ አለው ለማለት ይሆን? አላውቅም ትክክለኛ ትርጉሙ የቱ እንደሆነ፡፡ ግን ሁለቱም ልክ ይመስሉኛል፡፡

«ወሬ ወርቄ» የሚባል ዓይነት አንዳንድ ሰው አለ፡፡ አሳምሮ የሚያወራ - ወሬ ወርቁ አሳምሮ የሰለቀውን ለአንድ እንጀራ ልኩ ብትሰጠው፣ ከጉሮሮው ችሎ አይወጣለትም፡፡ አንዳንዶች አሉ - ወሬ ለማሳመር የተፈጠሩ፡፡ አፍ የሚያስከፍቱ፡፡ ሌሎች ግን አለን፡፡ ተገደን የምናወራ፡፡ እና አፍ ቀርቶ፣ እግዜር የከፈተውን ጆሮ ለማስከፈት ስናንኳኳ የምንውል፡፡ የማውራት ዝግመት አለብኝና «ታገሱኝ» ብዬ ነው የምጀምረው፡፡

ወሬዬን ጀመርኩ፡፡ የማወራው ስለ ህንድ አይደለም፡፡ ስለ ህንዱ ጋንዲ ማለቴ ነው፡፡ ይህ የጋንዲ ታሪክ አይደለም፡፡ የጋኒ ታሪክ ግን ነው፡፡ ጋኒ፡፡ አፍጋኒስታን ያበቀለችው፡፡ አሜሪካ ኮትኩታ ያሳደገችው፡፡ ዶክትሬቱንም፣ የዓለም ባንክ ዘናጭ የአማካሪነት ሥራውንም፣ የአሜሪካ ዜግነቱንም የሰጠችው፡፡ ዶክተር ፕሮፌሰር አሽራፍ ጋኒ፡፡

አሽራፍ ጋኒ ይህን መጽሐፍ የጻፈው ክሌር ሎክሃርት ከተባለች የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ጋር ተጣምሮ ነው፡፡ ይቺ ሴትዮ ኋላ ላይ፣ የሴፕቴምበር 11ዱን ጥቃት ተከትሎ፣ በኔቶ-አሜሪካን የበቀል እርምጃ ተንኮታኩተው ሀገር-ጥለው የሸሹትን ታሊባኖች፣ ማን ይተካቸው የሚለውን ለመወሰን በተለያዩ የአፍጋን የጦር አበጋዞች (እና ፖለቲከኞች) የተፈረመውን፣ ‹‹የቦን ስምምነት›› እየተባለ የሚታወቀውን፣ ያረቀቀችው ሴት ናት፡፡

ይህቺ ጠበቃ ሴት፣ በአፍጋንና በመላው ዓለም አዘቅት ውስጥ የገቡና በቁማቸው በመፈራረስ ላይ ያሉ ሀገሮችን እንዴት ማዳን እንደሚቻል ምክር የሚሰጥ ዓለማቀፍ ተቋምም ከአሽራፍ ጋኒ ጋር ተጣምራ በሽርክና የከፈተች ሴትዮም ናት፡፡ ለጊዜው ግን ትኩረቴን ከዚህች ከክሌር ሎክሃርት ላይ ላንሳና ወደ ዋናው ባለ ጉዳዬ ወደ አሽራፍ ጋኒ ላዙር፡፡

አሽራፍ ጋኒ - መዓት የዓለም ባንክ የኢኮኖሚ ፖሊሲዎችን የቀመረ እየተባለ ሲቆለጳጰስ ለሰማ ሰው - ይሄ ሰው ኢኮኖሚስት ይሆን? ወይስ ምን? ብሎ መጠየቁ አይቀርም፡፡ አሽራፍ ጋኒ ኢኮኖሚስት አይደለም፡፡ ግን አሜሪካ አምናብህ የኢኮኖሚ ውሳኔዎችን እንድትወስን ወይ እንድታማክር ከሾመችህ - የዓለም ባንክ ወሳኝ ሰው ትሆናለህ፡፡ የዓለም ባንክ ብቻ አይደለም፡፡ የአፍጋኒስታንም የገንዘብ ሚኒስትር ትሆናለህ፡፡ እንደ አሽራፍ ጋኒ፡፡

አሽራፍ ጋኒ የኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ የcultural anthropology አካዳሚሽያን ነበር፡፡ ባለፈው ያነሳናቸው የ60ዎቹ የሃርቫርድ ምሁራን ምክር - ወደ አሜሪካ መንግሥት ሰዎች - ታስታውሱ እንደሆን - በዚያ ምክር መሠረት በአሜሪካ የውጭ ፖሊሲ ትልቅ ትኩረት ከተሰጣቸው የዕውቀትና ምርምር ዘርፎች አንዱ ነው ይህ ካልቸራል አንትሮፖሎጂ የተባለው ከነባሩ አንትሮፖሎጂ ላይ የተጨመረ ፊቱን ወደ ባህሎች ያዞረ ሳይንስ፡፡

ካልቸራል አንትሮፖሎጂስቶቹ የሚያጠኑት ምንድነው? በዓለማችን የሚገኙ የተለያዩ ባህሎችን ቋንቋዎች ስነልቦና ነው፡፡ ቋንቋዎቹ ውስጥ ተሸጉጠው ያሉት፣ የእያንዳንዱን የቋንቋውን ተናጋሪ ስነልቦና፣ እሴቶችና፣ ዓለምን የሚረዳበትን መንገድ የሚጠቁሙት አመላካች ነገሮች ምንድናቸው? ብለው ነው የሚያጠኑህ የባህል ተመራማሪ አንትሮፖሎጂስቶቹ፡፡

ለምሳሌነት ዶክተር ዶናልድ ሌቪን የተባለ ኢትዮጵያ መጥቶ ወደ መንዝ በመውረድ አማራን አጥንቼያለሁ ብሎ መጽሐፎችን የጻፈውን አሜሪካዊ አጥኚያቸውን ግኝት ልጥቀስልህ፡፡ እንደ እርሱ አባባል፣ በአማራ ባህል ለወንድ ልጅ የሚወጡ ስሞች «እርገጤ» «ኩራባቸው» «ሽናባቸው» «በለው» «አንበሴ» «ነብሮ» «ግሥላ» «ደምመላሽ» «ጌታነህ» «አይተንፍሱ» ወዘተ የሚሉት፣ በባህላችን ውስጥ ያለውን የጦረኝነት አስተሳሰብ የሚያመለክቱ ናቸው፡፡

ይህን እኮ የምልህ ከግምት ተነስቼ አይደለም፡፡ Wax and Gold ብሎ በሰየመው በሰውየው መጽሐፍ ውስጥ ቃል በቃል የሰፈረውን ነው በምሳሌነት የምጠቅስልህ፡፡ እና ግን፣ ቆየኝማ አንዴ! ይህ የዶናልድ ሌቪን ግኝት ለአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ሲደርስ ምን ትርጉም ይሰጣቸዋል?

እንግሊዞች ሲያነቡትስ? ጀርመኖች ሲያነቡንስ? ለምንስ አገልግሎት ይጠቀሙበታል? ከጦረኝነታችን አንጻር ተነስተው ምን ዓይነት ፖሊሲ ያራምዱብን ወይም ያራምዱልን ይሆን? እኔ እንጃ! እኔን ለምን ታደርቀኛለህ? ከአሜሪካ ጋር አታነካካኝ ወንድሜ! እዚያው ራስህን ቻል!

መቼም በየመሐሉ ያገሬ ነገር እየጎተተ ያስለፈልፈኛልና ይቅርታ፡፡ ስጀምርም ታገሰኝ ያልኩህ ይህንኑ አመሌን አውቄ ነበር፡፡ አሁን እሺ ወደ ጀመርነው አንትሮፖሎጂስቱ ዶክተር አሽራፍ ጋኒ ወሬ ልመለስ፡፡

የአሜሪካ መንግሥት ለፖሊሲዎቹ ስኬታማነት - ካልቸራል አንትሮፖሎጂስቶችን በሚፈልግበት በዚያው ተመሳሳይ ምክንያት የተነሳ - የአሜሪካ መንግሥት በቀጥታም ሆነ በእጃዙር እንደሚዘውረው የሚታወቀው የዓለም ባንክም በበኩሉ - በዎልፌንሰን የፕሬዚደንትነት ዘመን - ካልቸራል አንትሮፖሎጂስቶችን በፖሊሲ አማካሪነት መቅጠር ፈለገ፡፡ ለምን?

‹‹ለምን›› ጥሩ ጥያቄ ነው፡፡ ምክንያቱማ - የዓለም ባንክ በየዓመቱ በድህነት አረንቋ ለተዘፈቁ ደሃ ሀገሮች፣ በኢኮኖሚ ቡጢ ለተንገዳገዱ (እና የኃያላኑን ደጅ ለጠኑ) ታዳጊ ሀገሮች ገንዘቡን በቢሊዮኖች ዶላር ይፈጠፍጣል፡፡ ግን ጠብ የሚል ለውጥ የለም፡፡ ብዙዎቹ አሁንም ባሉበት የድህነትና የመፍረክረክ ደረጃ ላይ እንደተጎለቱ ናቸው፡፡ እንዲያውም ብዙዎቹ ብሶባቸዋል፡፡

በዚህ መጽሐፍ ላይ የዓለማችን አንድ አምስተኛ የሚሆነው ሕዝብ - ማለትም ከ40 እስከ 60 በሚደርሱ ሀገሮች ውስጥ የሚኖረው - ቁጥሩ ከ1.5 ቢሊየን በላይ የሆነ የዓለማችን ሕዝብ - የዓለም ባንክን የገንዘብ እርዳታ ቅርጥፍ አድርጎ እየበላም፣ ግን አሁንም የዛሬ 50 ዓመት ከነበረበት የድህነት ወለል ፈቅ አላለም፡፡ ምክንያቱ ምንድነው?

ብዙዎች - እርዳታ ሀገርን አይለውጥም፣ ህዝብን አይታደግም፣ እና ይቅር - ብለው ‹‹ምቀኞች›› የሚያስብላቸውን፣ እርዳታ የሚባል ነገር ከናካቴው መቅረትን ሰብከዋል፡፡ ሌሎች ደግሞ ችግሩን ከአበዳሪ ተቋማቱ መሬት ላይ ጠብ ከማይል አስገዳጅ የኢኮኖሚ ቅድመ-ሁኔታዎችና፣ እያጎረሱ የየሀገሩን የሀብት ገበታ ከመቦጥቦጥ ሴራ ጋር ያገናኙትና ጥፋቱን በሰጪዎቹ ላይ ያላክካሉ፡፡

ሌሎች ደግሞ - ተቀባዮቹ የዓለማችን ሀገሮች ሁሉ - በሙስና የነቀዘ ሥርዓት የነገሠባቸው፣ ባለሥልጣኖቻቸው የገንዘብና የኑሮ ጠኔ ያጠናገራቸው፣ ነፃነትና ተጠያቂነት ያልዳበረባቸው፣ ሀገርን ለመለወጥ የሚያስችሉ ጠንካራ ተቋማት ያልተዘረጉባቸው፣ ጥቂት ጉልበተኞች እንዳሻቸው ወዳሻቸው የሚጋልቧቸው ረጋ-ሰራሽ ሥርዓቶች በመሆናቸው ነው - በማለት - ሁሉንም ተጠያቂነት በተቀባዮቹ ላይ ደፍድፈው ተቀምጠዋል፡፡

እነዚህን ሁሉ ለአሰርት ዓመታት ያስተናገደው የዓለም ባንክ - በመጨረሻ - ከታወቁ የዓለማችን ዩኒቨርሲቲዎች የወጡ - አፍና ጆሮ የሚያስከፍቱ - እንደ አሽራፍ ጋኒ ያሉ እሳት የላሱ የባህል ምርምር የቀለም ቀንዶችን አመጣና አጥኑልኝ አላቸው፡፡

እስቲ እርዳታ ተቀባዮቼ ሀገሮች፣ ህዝቦች፣ ሥርዓታቸው፣ የዘር፣ የጎሳ፣ የብሔር-ብሔረሰብ ስሪታቸው፣ የእድገት ደረጃቸው፣ ሐይማኖታቸው፣ ወዘተ ወዘተ... የምንሰጣቸውን እርዳታ በአግባቡ እንዳያውሉት - አሊያም እንዲያውሉት - የሚያደርግ አንዳች ፍንጭ ይገኝበት እንደሆን አጥኑልኝ - ብሎ - ገንዘቡን ከመልቀቁ በፊት - የእርዳታ ተቀባዮቹን ስነልቦና እንዲያጠኑለት በየሀገሩ አሰማራቸው፡፡

ዶክተር አሽራፍ ጋኒ - በየተላከባቸው ሀገሮች ሁሉ - በኔፓል፣ በአፍጋን፣ በሱዳን፣ ወዘተ ወዘተ.. በራሱ በዎርልድ ባንክ ፕሬዚደንት በዎልፌንሰን የፀደቁ የዓለም ባንክ ፖሊሲዎችን ሳይቀር - ከተቀባዩ ማህበረሰብ ባህልና አስተሳሰብ፣ የለውጥ ፍላጎትና የእድገት ፍላጎት ጋር ያልተጣጣሙ ናቸው - በማለት፣ በሰሉ ትችቶቹ ጥንብ እርኩሳቸውን አወጣቸው፡፡

በአበዳሪዎች ቤት መወዳደስና መሸፋፈን እንጂ፣ ልክ ልክ መነጋገር አልተለመደም ነበር መሰለኝ፡፡ እና በዚህ የተነሳ፣ ጥንብ እርኩሳቸውን ሊያወጣ የተመደበባቸውን - የባህል ቆፋሪውን ጋኒን - ሁሉም የዓለም ባንክ የሥራ ባልደረባ ጥርቅም አድርጎ ዘጋው! ሳስበው - እንጀራዬ አይዝጋኝ - ብሎ ‹‹ኢግኖር የሰፋቸው›› ይመስለኛል፡፡ በሠራተኛው፣ በኢኮኖሚስቱ ሁሉ የተጠመደውን ሰው ግን፣ ፕሬዚደንቱ ከልቡ ወደደው! አሁን ገና ልክ ልኬን የሚነግረኝ የሀቅ ሰው አገኘሁ ብሎ፡፡ መሰለኝ፡፡

(‹‹መሰለኝ›› ያልኩት፣ ጄምስ ዎልፌንሰን ሥልጣን ከለቀቀ በኋላ በጻፈው መጽሐፍ ስለ ጋኒ የሰጠው ምስክርነት የሚናገረውን አስታውሼ ስለተናገርኩ ነው! ምስክርነቱ ምን ያክል እውነት ነው? ዎልፌንሰን ራሱ የHarvard ቅጥቅጥ ነውና፣ የ Columbia ቅጥቅጥ የሆነ እኩያውን ሲያገኝ፣ ገና እንዳየው ዓይነ-ውሃውን ወዶለትም ይሆናል፣ ማን ያውቃል? አንድዬ ይወቅለት! ግን ራሱ ዎልፌንሰን - በመጨረሻ ለሚስትህ ያልተገባ ጥቅም አስገኝተሃል ምናምን ተብሎ ከሥልጣን የለቀቀ መሰለኝ - የሞተ አይወቀስምና አሁን ወደ ጋኒ!)

ጋኒ ከ60ዎቹ ጀምሮ ከሀገሩ አፍጋኒስታን የወጣ ምሁር ነው፡፡ እና በሁለነገሩ ፈረንጅ ሆኗል፡፡ ክርስትያን ሚስት አግብቶ ሁለት ልጆችን ወልዷል፡፡ ብዙ የትውልድ ሀገሩ ሰዎች ራሳቸው እንደ አሜሪካዊ ይቆጥሩታል፡፡ ፈረንጆቹ ራሳቸው አፍጋኒስታናዊነቱን ረስተውታል፡፡ ብቻ ግን ብዙ ጊዜ በመስክ ሥራ ወደ አፍጋኒስታን ላኩት፡፡

ጋኒ ብዙ ዓመታት ከዚህች ደራሲት አቮካቶ (ጠበቃ) ጋር ተጣምሮም ብዙ ምርምሮችን በአፍጋን ላይ እንዲሠራ አደረጉት፡፡ በመጨረሻም ታሊባኖች በአሜሪካኖች ጥምር ሃይል ከተወገዱ በኋላ በተተከለው በሃሚድ ካርዛይ መንግሥት ውስጥ፣ አሽራፍ ጋኒን የገንዘብ ሚኒስትር አድርገው ሾሙት፡፡ ወይም አሾሙት፡፡ የውጪ መንግሥታት ሆነው ሳለ - እንዴት ‹‹ሾሙት›› እና ‹‹አሾሙት›› የሚሉ ቃላትን ተጠቀምክ? የሚለኝ ካለ - አሁንም አታነካካኝ፣ ራስህን ቻል ብለው ደስ ይለኛል፡፡

ግን ችግር የለውም፡፡ እነግርሃለሁ ምክንያቴን፡፡ ብዙዎች ከታሊባኖች ከሥልጣን መነሳት በኋላ ጀምሮ እስከ አሁኑ የታሊባኖች ዳግም ሥልጣን ድረስ በአፍጋን የቆየውን የመንግሥት አስተዳደር - አሻንጉሊት መንግሥት ብለው ስለሚጠሩት ነው፡፡ አሻንጉሊት መንግሥት ካለ፣ የባለሥልጣኖቹን ማንነት የሚወስኑት፣ ባለ አሻንጉሊት ፋብሪካዎቹ ናቸው፡፡ የሚስማማቸውን ዓይነት አሻንጉሊት ሰርተው ፕሮሞሽን ይሰሩለታል፡፡ ያዳንቁለታል፡፡ ለስልጣን ያጩታል፡፡

ያ እነርሱ ያቀረቡልህ አሻንጉሊት ካልተመረጠ፣ ወይም እገሌ ወይም እገሊት የተባለችው አሻንጉሊት ሥልጣን ላይ ካልቆየ/ች፣ ሃባ ሳንቲም የለም! ግፋ ሲልም የጦር ጄቶችና ክሩዝ ሚሳይሎች ድምጾች በጆሮህ ያፏጩብሃል! እና ከእነዚህ ዓይነቶቹ ዓይን ያወጡ ‹‹አሻንጉሊት መሪዎች አቅራቢዎች›› ጋር ደፍረህ አፍ-ለመከፋፈት - ወይ በባህል ቆፋሪዎች ተጠንተህ ያበቃልህ፣ የወጣልህ ተናዳፊ ‹‹ጦረኛ›› ሰው ወይም ህዝብ መሆን አለብህ መቼም!

(እንጂ የዋለለ የእንቧይ ካብ የመሰለ በሞት-አፋፍ ላይ ያለ ሀገር ላይ ቆመህ፣ ወይ እፍ ቢሉህ የምትወድቅ የዜጋህ ድጋፍ የጠመመብህና የነጠፈብህ ዓይነት መናኛ ባለሥልጣን ሆነህ፣ ከአሻንጉሊት አቅራቢዎችህ ጋር እምቢ-እሺቆይ እያልክ አትሳፈጥም በጤናህ!)

ለማንኛውም፣ እጅግ አወዛጋቢ በተባለ ምርጫ፣ ሀገሩን ለመምራት ሲል አሜሪካዊ ዜግነቱን ትቶ፣ ዘመናዊ አልባሳቱን ትቶ፣ ወደ አፍጋን የገባው ዶክተር አሽራፍ ጋኒ፣ በአሜሪካ አደራዳሪነት፣ በምርጫው አልተሸነፍኩም ከሚለው ተፎካካሪው ከአብዱላህ አብዱላህ ጋር ጥምር የአፍጋን መንግሥት ለመመስረት ተስማምቶ፣ ሁለቱም ‹‹እኩላዊ›› ድምጽ ነው ያገኙት በሚል ቃል - የፕሬዚደንትነት ውል አሰረ፡፡

(አንድ ጆርጅ ፓከር የተሰኘ የኒው ዮርከር ጋዜጣ ተንታኝ፣ ‹‹እኩላዊ›› የሚለው ቃል በአፍጋን ቋንቋ ያልነበረና፣ ለዚሁ ጋኒንና አብዱላህን ለማስማማት ተብሎ አዲስ የተፈጠረ ቃል ነው - በማለት ይሳለቅበታል! - ይህን ‹‹እኩላዊ›› የሚል ቃል ስሰማ የኛ ሀገሩ ‹‹ልማታዊ›› የሚል አዲስ ቃል ትዝ አለኝ፡፡ ‹‹ልማታዊ›› የሚል ቃል - እርግጠኛ ነኝ - በአለቃ ኪዳነወልድ ክፍሌም ሆነ በከሣቴብርሃን መዝገበ ቃላት የምናገኘው ቃል አይመስለኝም! ኧረ በህግ አምላክ! ስንቱን ረገጥኩ? ኧረ ወደ ገደለው ጎበዝ!)

አሽራፍ ጋኒ - ታሪኩና ተሞክሮው፣ የሥልጣን ጉዞውና አጀማመሩ ይህን ይመስላል፡፡ አጨራረሱን ሁላችንም ያየነው ስለሆነ አልደግመውም፡፡ ለማኝ ካካውን ሳይጥል፣ ገና ወፍ ሳይንጫጫ ተነስቶ፣ ከዋና ከተማዋ ካቡል፣ ሰው ሳያየው፣ ወፍም ሳያየው፣ ‹‹እግሬ አውጭኝ›› ብሎ፣ ወደፈረደባቸው አሜሪካኖች ‹‹እብስ›› ያለበትን አሰቃቂ የፍርጣጤ መንገድ ማለቴ ነው፡፡

(ከመንጌ ወዲያ ይሄን ‹‹መፈርጠጥ›› የሚሉትን ቃል፣ ለጠላቴም አልመኘው! ግን ታሪክ ይደጋገማልና፣ በየመጣው በየሄደው አምባገነንና አሻንጉሊት ሁሉ ላይ እየተደጋገመ እናየዋለን! ያሳዝናል፡፡

ለማንኛውም አሽራፍ ጋኒ ሀገሩን ሊመራት ያሰበው፣ ከሥልጣኑ 8 ዓመታት ቀደም ብሎ ከክሌር ሎክሃርት ጋር በጻፈው በዚህ የጥናት ሥራው መሠረት ነበር፡፡ ምኞቱ ይሄ ነበር፡፡ ወይም ‹‹ወሬው›› እንበለው? አዎ ወሬው በዚህ መጽሐፍ እንደተገለጸው ነበር፡፡ የሰው ልጅ መጨረሻውን ቢያውቀው፣ ከማውራት ይቆጠብ ነበር ይሆን እላለሁ አሁን - አፍጥጬ እያየሁት ይሄን የጋኒን መጽሐፍ፡፡

በዚህ መጽሐፍ የምናገኛቸው የጋኒ ወሬዎች አፍ ያስከፍታሉ፡፡ ምዕራፍ ሰባት፡፡ ‹‹ስኬታማ መንግሥት ማከናወን ያለበት አስሩ ቁልፍ ተግባራት››! ይላል፡፡ እኔ ድሮም አስሩ፣ ሃያው፣ አርባ ስምንቱ፣ ጂኒው ጃንካው እያለ ነገሮችን በቁጠር ሰፍሮ የሚያስቀምጥ ሰው አይጥመኝም - ብዬአለሁ፡፡ የሰው ልጅ፣ የሰው መንግሥት፣ ብዙ ነው መንገዱ፡፡ አስሩ፣ ሃያው፣ ሰላሳው እያለ መስፈርና መቁጠር ምን አስፈለገው? - ወሬ ነዋ! (ልበለው ይሆን?! የወደቀ ዛፍ ያው ምሣር ይበዛበታል መቼም - ነገር አያምርለትም!)

አንደኛ፡፡ መንግሥት የአስተዳደር ሥራውን አውቆ ሠርቶ መገኘት፡፡ (የሚያስቀው ጋኒ አስተዳደሩን አልቻለበትም!)፡፡ ሁለተኛ፡፡ የገበያውን እንቅስቃሴ ያለ እንከን ማስኬድ፡፡ (ጋኒ በመሪነትም እያለ የአፍጋን ገቢ ሁለት ነገር ነው - ሃሺሽና የእነ አሜሪካ እርዳታ!)፡፡ ሶስተኛ፡፡ ከሁሉ ነገር በፊት የሀገርን ፀጥታና የህዝቡን ደህንነት ማረጋገጥ፡፡

(ጋኒ ካቡል በሚገኘው ጥንታዊው የጉል ካና ቤተመንግሥቱ ቁጭ ብሎ 7,000 (ሰባት ሺህ) መጻሕፍቶቹን ያካተተ ዘመናዊ ቤተመጽሐፍት ሲያደራጅ፣ ታሊባኖች ከታቡል በስተምዕራብና በስተሰሜን ጦራቸውን አደራጅተው አራት ወረዳዎችን ተቆጣጥረዋል!)፡፡

አራተኛ፡፡ የመንግሥትን ኢንፍራስትራክቸር (የመሠረተ ልማት አውታሮች) ያለአንዳች መዝረክረክ መገንባት፡፡ (ጋኒ ከህንዱ ናሬንድራ ሞዲ ጋር ተገናኝቶ ሲመለስ፣ ለህዝቡ በቲቪ ቀርቦ፣ ህንዶች በቀጣዩ ሁለት ዓመት 20 ቢሊየን ዶላር ኢንቬስት ሊያደርጉ ስምምነት አድርገናል - ብሎ መግለጫ ይሰጣል፣

የካቡል መንገዶች ላይ የምግብ ዘይትና የዳቦ ስንዴ ያጡ 26 ሺህ አፍጋናውያን በቁጣ ንቅል ብለው ወጥተው ቤተመንግሥቱ በር ላይ እየጮሁ፣ እሱ ወጣት አማካሪዎቹን ሰብስቦ፣ በቀጣዮቹ 25 ዓመታት ሊሳኩ የሚችሉ ሜጋ ፕሮጀክቶችን፣ በቢሊዮን ከነሚቆጠሩ ባጀቶቻቸው፣ እነሱ በፕሮጀክተር ታግዘው እያቀረቡለት፣ እርሱ እየገመገመ በደስታ ተመስጦ ያሳልፍ ነበር!)፡፡

አምስተኛ፡፡ የህግ የበላይነት ላይ፣ ህግን ማስከበር ላይ፣ (Rule of Law & Law Enforcement) አንዳችም ሰፋጣ መኖር የለበትም፡፡ (አሽራፍ ጋኒ ግን፣ እንኳን በአፍጋን ሙሉ ይቅርና፣ ዋና ከተማዋ ካቡል ውስጥ ራሱ የሚገኙ የአሜሪካና የሌሎች ኤምባሲዎችን፣ እና የራሱን ቤተመንግሥት ከአጥፍቶ ጠፊ አፈንጂዎች መከላከል ተስኖት፣ ግማሹ የከተማው ክፍል ቀን ቀን ለሰላማዊ መንገደኞች ዝግ ሆኖ ነው የሚውለው፣

የአሜሪካ ኤምባሲ የኔቶ ሄሊኮፕተሮች እያንዣበቡ እየቃኙት ነው የሚውሉት፣ እና በአራቱም የሀገሪቱ አቅጣጫ ሰዎች በቪዲዮ እየተቀረፀ ይሰየፋሉ፣ ይቃጠላሉ፣ ይበለታሉ፣ አንዴ አስራ-ስድስት ሰዎች በአክራሪዎች ታግተው አካላቸው ተጨፍጭፎ ሲለቀቅ፣ ህግን ማስከበር ብቻ ሳይሆን፣ ማን ምን የት እንዳደረገ ማየትም ማወቅም የተሳነው መንግሥት ነው የሆነው የጋኒ መንግሥት!)፡፡

ስድስተኛ፡፡ የመንግሥት ትልቁ ሀብቱ ሰው ነው፡፡ ዜጋው ነው፡፡ እና የሰውን ካፒታል (Human Capital) ታይቶ በማይታወቅ መልክ ማሳደግ፡፡ ይሄ የአሽራፍ ጋኒ መጽሐፍ በተለይ ትልቁ ዲስኩሩ፣ ከከሸፈች ሀገር ውስጥ፣ አዲሲቷን ተስፋ ያላትን ሀገር ለማዋለድ፣ በታሪክ ታይቶ የማይታወቅ፣ በወጣት የተማሩ የሀገር ልጆች የተገነባ የዕውቀት ሠራዊት ሀገሪቱን እንደሚያጥለቀልቃት ይደሰኩራል፡፡

የጋኒ አድናቂዎችም ብዙዎቹ የኮሌጅ ተማሪ የሆነ፣ የእርሱን የኮሎምቢያ ዱክትርና፣ የጆን ሆፕኪንስ መምህርነት፣ የበርክሌይ ፕሮፌሰርነት፣ የካቡል ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰርነት አድንቀው ‹‹እንደ አንስታይን›› ጭራውን የሚከተሉ ወጣቶች ነበሩ፡፡

ግን በጣም የሚያስቀው፣ በጋኒ መሪነት ወቅት፣ ገና 30 ዓመት ያልደፈናቸው አሜሪካና እንግሊዝ የኖሩ አፍጋኖችን አማካሪና አምባሳደር አድርጎ ሲሾም፣ ያገሩ የተማሩ ወጣቶች፣ ሌላ ቀርቶ፣ ፖላንድ የተሻለች ሠላም የሰፈነባት ሀገር ሆና ተገኝታ፣ በያመቱ ወደ ፖላንድ እስከ 140ሺህ አፍጋኖች ይሰደዱ ነበር፡፡ የሂዩማን ካፒታሉ ወሬ፣ በተግባር በBrain Drain ነው የተጠናቀቀው፡፡

አንዱ ጋኒን የሚያውቀው የዩኒቨርሲቲ ሠራተኛ ያየውን ሲናገር፣ ጋኒ በካቡል ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ተብሎ ከመጣ በኋላ ሲሠራ ያየሁት ሁለት ነገር ነው፡- አንድም ሠራተኛውንና መምህሩን ሁሉ በቡድን እየሰበሰበ የንዴት ኃይለ ቃላት መዓት ሲያወርድባቸው፣ የሚጮህበት ሰው ካጠገቡ ከሌለ ግን፣ ወጣቶችን ሰብስቦ፣ ፈጽሞ ሊያደርገውና ሊተገብረው የማይችላቸውን ነገሮች ቃል ሲገባላቸው ነው! ከእነዚህ ሁለት ነገሮች ውጪ ሌላ ነገር ሲያደርግ አገኘሁት ያለ ካለ ክሰሰኝና በፈቃደኝነት እታሰራለሁ!

ሰባተኛ፡፡ ስምንተኛ፡፡ ዘጠነኛ፡፡ አስረኛ፡፡ ሁሉንም፡፡ አሽራፍ ጋኒ ሲያወራቸው፡፡ አሽራፍ ጋኒ ሲጽፋቸው፡፡ አሽራፍ ጋኒ ሲያጋንናቸው፡፡ አቤት! አቤት! አቤት ማማራቸው! ስምንተኛው የመንግሥት ግዴታ፣ የሁሉንም ዜጎች ተሳትፎ - ሙሉ በሙሉ ማረጋገጥ የሚል ነው፡፡ ልክ እኛ ሀገር ‹‹መደመር›› እንተባለው ማለት ነው፡፡ ወይም ልበለው ይሆን?

በጣም የሚገርመው ግን - መጀመሪያ ዶክተር አሽራፍ ጋኒ በምዕራብ ሸሪኮቹና ተስፋ በጣሉበት ወጣቶች በተሠራለት ፕሮሞሽንና በተሰጠው ከፍ ያለ ግምት የተነሳ፣ በመሪነት ወንበር እንደተቀመጠ በህዝቡ የተቸረው የተቀባይነት ደረጃ፣ ወደ 81 ፐርሰንት ተመንጥቆ ነበር፡፡ ገና አስር ወር ሳይሞላው፣ አኪሩ ሁሉ እንደ ሰሊጥ ረገፈና፣ የተቀባይነት ደረጃው፣ በህዝብ አስተያየት ምዘና፣ 23 ፐርሰንት ብቻ ቀረ፡፡ በስተመጨረሻ ከእርሱም የቀረለት 3 ፐርሰንት ብቻ ነበር፡፡

ሌላውን የሩቁን ሰው ተወው! ካቢኔው ራሱ በጋኒ አላመነበትም፡፡ የፓርላማው አባላት እርሱ ሲናገር፣ አብረው አይናገሩም፡፡ አይመልሱም፡፡ አይስቁም፡፡ ልክ እንደ ሮቦት ስሜት አልባ እንቅስቃሴ ነው የምታይባቸው፡፡ ይላል ገና በ2016 አስቀድሞ የጋኒን መጨረሻ የተነበየው የኒውዮርከሩ ተንታኝ፡፡

ጋኒ በፓርላማው ሪፖርት ሲያርብላቸው የስሜት ግንኙነት ሲፈጥር የምታየው ሰው የለም፡፡ አንዳንዶቹ በጣቶቻቸው ጉንጮቻቸውን ይፈትላሉ፡፡ ሌሎች አቀርቅረው ኖት ይይዛሉ፡፡ ልክ በክፉ መምህር ፊት እንደተቀመጡ ተማሪዎች፡፡

እና አንድ የአፍጋን ምሁር ለጋኒ አዝኖለት መሰለኝ ሲደመድም - ጋኒ ብቻውን ነበር ማለት ይቻላል፣ በሁሉ ነገሩ ተነጥሎ ብቻውን ቀርቶ ነበር፣ ብቻውን ነው የሚዳክረው፣ በዕውቀት ብቻውን ነው፣ በጥረት ብቻውን ነው፣ በህልም ብቻውን ነው፣ እርሱ የወደፊቱን ሲያልም፣ ሩቡን መንገድ ራሱ ሄዶ የሚያግዘው የለም፣ እርሱ ለአፍጋኒስታን ያየውን ወይም የታየውን ያየለት ማንም ሰው የለም፣ አንጀቴን በልቶታል! - በማለት የስላቅም፣ የትካዜም፣ የቅኔም የሚመስል ሾርኔውን ቸሮታል፡፡ ሳስበው - ብቻውን ከቀረኮ - ወሬውና ተግባሩ አልገጥም ካለኮ - አፍጋን ላይ ተቀምጦ ስለ ዲዮጋን እየቃዠ ከነበረኮ - ሰውየው - የሆነ ብሎን አላልቶ ነበር ማለትኮ ነው!!

ለወሬና ለስላቅማ ማን ብሎን! ማን ብሎኝ! የሰው ነገር በቃኝ አቦ አሁንስ! አበቃሁ! ቻው ሠላም!

  . . . ሁሉን ነገር ካስተዋሉት ያስገርማል። የኑሮ ትንሽ የለውም። እዛ የወደቀችው ሳር አስገራሚ ናት። ወፍ ለቅሞ ጎጆ ይሰራባታል። ይሄን ሳር አጭዶ ያመጣው ማጭዱ አስገራሚ ነው። ሰዎቹ ...
12/05/2022



. . . ሁሉን ነገር ካስተዋሉት ያስገርማል። የኑሮ ትንሽ የለውም። እዛ የወደቀችው ሳር አስገራሚ ናት። ወፍ ለቅሞ ጎጆ ይሰራባታል። ይሄን ሳር አጭዶ ያመጣው ማጭዱ አስገራሚ ነው። ሰዎቹ ማጭድ ማሰባቸው?! .. ሳሩን አጭዶ ያመጣልኝ ሰውዬ ዘገየ ይባላል። ጨዋታ ያውቃል። እሱ ሲያወራኝ የሚገርም ነው ታሪኩ። 'ለምን?' ብትል እንዳው ወንድ ሆነ እንጂ ታሪኩ ተኔው አንድ ነው።

የእኔ ታሪክ ምንም ብለፋ፣ ምንም ብቀባጥር የእኔ ብቻ አይሆን። 'ለካ የእሱ የእኔን ይመስላል!' ብለህ መታዘብ አለ።

ያንተ የአንተ ተሆነ፣ የእናትህ የእናትህ ተሆነ፣ የሰብለ የሰብለ ከሆነ፣ እንዴት እዝህ ደረስን? እሱ እኮ ነው!

***

ጠዋት እዚህ ፀሐይ ስሞቅ የቆረጥኩት የአውራ ጣቴ ጥፍር ለስንት ጉንዳን እራት ይሆናል?
ባላርስም አበላሁ ማለት አይደል? . . .

****
ፊታውራሪ መሸሻ ሰብለን አባረሩ። ጣሊያን እኔና ሰብለን፣ ሳርኪስን አባረረ። ሳርኪስ ሞተ። በዛብህ ሞተ። በመሸሻና በሞሶሎኒ መሃል ልዩነቱ ምንድን ነው? በኮሪያና በተማሪ ድንጋይ መሃልስ?
የዕውን ላስብ ብትለው አያሳስብም? . . . .

***
ነፃነት ተመለሰ። ያም ወሬኛ ንጉስ ነኝ ብሎ። እንግሊዝ እየነዳ አመጣው። ገረሱን አያደርጉትም ነበር? በላይን አያደርጉትም ነበር? አበበ አረጋይስ? ዞሮ ዞሮ ማን? እሱ!!
እድሮው መሬቴና ቤቴ ተመለስን። ጎጆዬ ፈርሳ የጣሊያን መኮንን ይሄን ሕንፃ ሰርቶበት አገኘሁ። ቤቱ ይበርደኛል፣ ይሸተኛል። አየር አያስገባ!! ይኼው አድሬበት አላውቅም። ከጀርባ ያለው ጭቃ ቤት ነው የምተኛው . . .

ብርዱን አልቻልኩትም። ቁርጥማቱ አላስተኛ አለኝ። ጭቃ ቤት ነው ለኔ የሚሆነኝ። ገና ለገና ፈረንጅ የሰራው ቤት ልኑር ብዬ ዕድሜዬን አላሳጥርም . . .

****

እኛ ሀገር ከአመት አመት ጦርነት ነበር ልጄ።
ስንቷ በሙሽርነቷ ቆማ ቀርታለች? እኔም አንዷ አይደለሁ?
ስንቷ ባሏን፣ ስንቷ የከንፈር ወዳጇን አጥታለች? ቤቱ ይቁጠረው።
ስንቱ ሎጋ አካለ ስንኩል ሆነ? ባሌ የነበረው የአሰፋ አባት (ሱባ ተጠናሁ በኋላ አግብቼው .... ማግባት ነው እንዴ?) የእኛው አላንስ ብሎ በሌላ ሰው ነገር ገብተን፣ ኮርያ ሄዶ ታሞ መጣ።
ብዙ አልቆየም ሞተ . . .

እናልህ ለሌላ ቆስሎ መሞት ምን የሚሉት ዘዬ ነው? እኔ አሁን ኮርያ የሚባል ሀገር ይኑር አይኑር በምን አውቃለሁ? ለራሳችን አንሶ ለሰው ተርፈን። ወንድ በዝቶብን ነው እንደ ቡና ወደ ውጪ እንልክ የነበረው? ኮርያ ለኔ ምኔ ነው? ስንቱ ገበሬ በጥልያን ቡዋንብ ተመታ? ዓይኑ ታወረ? ስንቱ ነው 'መሶሎኒ' የሚባል ፈረንጅ የሚያውቅ? እንደው በመንገድ ተላልፈው 'ኖር' 'ኖር' 'ወያ' 'ወያ' ተባብለው ያውቃሉ?

ተዚያ በሶማል በኩል፣ ተዚያ በሐማሴን በኩል በየቦታው ጦርነት። ማን አዘዘ ይሄን ሁሉ?
አሁን ደግሞ በየትምሕርት ቤቱ ተማሪ ይራበሻል። እኔ ይኼን አልወድም። ባለፈው እዚህ የተወረወረ ድንጋይ አንድ የቦሊስ ዓይን አጠፋ። አንድ ዓይኑ ፈረጠ። እንዲህ እኛ ሰፈር ተንጋሎ ሲያጓራ ነው ያየሁት። የተመታበት ድንጋይ ልጅ የወረወረው አይመስል። ተመሃል ሆሆሆ እያለ የስንት ሰው ቤት ይፈርሳል? እስኪ ንገረኝ . . . .

***

. . . ራስህን ጥንካሬ አስተምር። የከብት ጥንካሬ ሳይሆን የሰው። የአህያ ሳይሆን የሰው። ፅናትና ስራ አንድ ላይ ጎን ለጎን ካልሆኑ ድንጋይ መሆን ነው። አለዛ ትገፋለህ፣ ገድ ይርቅሃል . . .

***

#መረቅ
Photo - Marthas_point

እውነተኛው የሐብት ምንጭውስጠ ሕሊና የሐሳብ ችግር (ድርቅ) የለበትም፡፡ በውስጡ እጅግ የበዙ እና ወደ ገንዘብ ሊለወጡ የሚችሉ ሐሳቦች አሉ፡፡ እውነተኛ ሐብት በአክሲዮን ብዛት አሊያም ባንክ ...
08/05/2022

እውነተኛው የሐብት ምንጭ

ውስጠ ሕሊና የሐሳብ ችግር (ድርቅ) የለበትም፡፡ በውስጡ እጅግ የበዙ እና ወደ ገንዘብ ሊለወጡ የሚችሉ ሐሳቦች አሉ፡፡ እውነተኛ ሐብት በአክሲዮን ብዛት አሊያም ባንክ ውስጥ ባለው ተቀማጭ ገንዘብ አይወሰንም፡፡ እነርሱ የሐብት ምልክቶች ብቻ ናቸው፡፡ እውነተኛ የሐብት ምንጭ፤ በራሱም ሐብት የሆነው አስተሳሰብ ነው፡፡ በችግር ውስጥ ያሉ ሰዎች ዘወትር የተሳካላቸው ሰዎች እንዳብጠለጠሉ ናቸው፡፡ የአንዱን ሥም እያነሱ ‹‹እርሱ አጭበርባሪ ነው›› ማለታቸው የተለመደ ነው፡፡ የሚፈልጉትን መልሰው ስለሚኮንኑ ነው የማይሳካላቸው፡፡ ሐብት በእኛ ደጅ እንዳይደርስ ለማድረግ ቀላሉ መንገድ ከእኛ የበለጠ ሐብት ያላቸውን ሰዎች መኮነን ነው፡፡

ከዂሉ በላይ ቅናት የድህነት ምንጭ ነው፡፡ ቅናትን ማሸነፍ ቀላል ነው፤ በሰዎች ስኬት ደስ መሰኘትና ከትልቅ ደረጃም እንዲደርሱ መመኘት ብቻ ነው፡፡

ቅናተኛ መሆን በጣም አደገኛ ነገር ነው ምክንያቱም አዕምሮን በአሉታዊ ሐሳቦች ይሞላዋልና፡፡ ስለዚህም ሐብት ወደ አንተ ሳይሆን የሚመጣው ከአንተ ነው የሚሸሸው፡፡ በሰዎች ስኬት ደስ መሰኝት አሉታዊ ሐሳቦችን ከማጥፋቱ ባሻገር በውስጥህ መልካም ስሜት የሚፈጥር በመሆኑ ስኬትን እንድትጎናፀፍ ያስችልሃል፡፡

ራስህን በእነዚህ ምክሮች አስታጥቅ

- በውስጠ ሕሊናህ ረዳትነት ሐብታም ለመሆን ወስን፤
- ላብህን አንጠፍጥፈህ ከልክ በላይ መድከም ምናልባትም ከሞት በኋላ ሊረዳህ ይችል ይሆናል፡፡ ሐብታም ለመሆን መፍጋት አይጠበቅብህም፤
- ሐብት የውስጠ ሕሊና እምነት ነው፡፡ የሐብትን ሐሳብ በአዕምሮህ ላይ አትም፤
- በየእለቱ ወደ መኝታህ ከማምራትህ በፊት ለአምስት ደቂቃ ያህል ‹‹ሐብት›› የሚለውን ቃል በጽሞና ብትደጋግም ውስጠ ሕሊናህን እውን ያደርገዋል፤
- የሐብት ስሜት ሐብትን ይፈጥራል፤
- አዕምሮህና ልቦናህ (ውስጠ ሕሊናህ) መስማማት አለባቸው፤
- በአዕምሮህ ውስጥ የሚመላለሰው ዋና ሐሳብ የሐብት እንጂ የድህነት ሊሆን አይገባውም፤
- ‹‹ንግዴ እየተሻሻለ ነው፤ በሐብት ጎዳና ላይም እገኛለሁ›› ብለህ በመደጋገም ንግድህን ማሻሻል ትችላለህ፤
- ወደ አዕምሮህ ባንክ የሐብትና የስኬት ሐሳቦችን ብታገባ ውስጠ ሕሊናህ ከፍ ያለ ወለድ ነው የሚያስገኝልህ፤
- እውነተኛ የሐብት ምንጭ አዕምሮህ፣ አስተሳሰብህ ነው፤
- ቅናትና ምቀኝነት የሐብት ጉዞን የሚያደናቅፉ ትልቅ ጋሬጣዎች ናቸው፤
- ሐብታም እንዳትሆን እንቅፋቱም በገዛ አዕምሮህ ውስጥ ያለው ሐሳብ በመሆኑ በመልካም አስተሳሰብ ግንቡን ደርምሰው፤

Address

Addis Ababa

Telephone

+251952060000

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Wisdom Ethiopia Books posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to Wisdom Ethiopia Books:

Share

Category