24/04/2026
ንጉስ ነጃሺ አክሱምና ዉቅሮ
✅✅✅✅✅✅✅✅
በአሕመዲን ጀበል፥ክፍል አንድ
🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴🔴
ይህ ጹሑፍ በትግራይ ጦርነት ጊዜ የነጃሺ መስጂድ ላይ ጥቃት በተፈጸመ ጊዜ ተጽፎ በሦስት ተከታታይ ክፍሎች በኔ በአሕመዲን ጀበል የፌስቡክ ገጽ እእና የግል ፕሮፋይል ላይ በጃኑዋሪ 2፥ 2021 ተለጥፎ ነበር። ዛሬም በድጋሚ ሦስቱ ክፍሎች በተከታታይ ይቀርባል። መልካም ንባብ።
🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁🎁
ነቢዩ (ሶ.ዐ.ወ) በእምነት ነጻነት፣ እጦት ጭቆናና መከራ ከባልደረቦቻቸው መከላከል እንደማይችሉ ሲገነዘቡ ወደ ሐበሻ ምድር እንዲሰደዱ መከሯቸው። እንዲህም አሏቸው፡-
‹‹ወደ ሐበሻ ተሰደዱ፤ በእርሷ አንድ ንጉሥ አለ። ከእርሱ ፊት ማንም ተበዳይ አይሆንም። … (ስለዚህ ተሰደዱ)፤ አላህ ካላችሁበት ሁኔታ አውጥቶ ድል እስክንጎናጸፍ ድረስ…፡፡››(ሙሐመድ ጦይብ ኢብን ሙሐመድ ኢብን ዩሱፍ፣ ኢትዮጵያ እና ኢስላም (ትርጉም)፣ ነጃሺ ማተሚያ ቤት፣ ገጽ 9)
ሰሀቦችም በሁለት ዙር ተሰደው ወደ ኢትዮጵያ-አክሱም መጡ፡፡በንጉስ ነጃሺ ዘንድ ነጻነትን ተጎናጸፉ፡፡ የነቢዩ ሙሐመድ (ሶ.ዐ.ወ) ባልደረቦች በሐበሻ የገጠማቸውን ሁኔታ እንዲህ ሲሉ መስክረዋል፡-
‹‹ሐበሻ ገባን። መልካም ጎረቤቶችንም አገኘን። በሃይማኖታችን ምክንያት የሚደረግብን ተፅእኖ አልነበረም። አላህንም በሰላም መገዛት ጀመርን። አንድም ችግርና መከራ አላጋጠመንም። የምንጠላውን ነገር አልሰማንም።››
(አህመዲን ጀበል፣ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ከ615-1700 የጭቆናና የትግል ታሪክ፣2003፣ገጽ 35)
መናገሻ ከተማውን አክሱም ከተማ አድርጎ ይመራ የነበረው ንጉስ ነጃሺ በኢስላም ኃይማኖት ታላቅ ስፍራ ከሚሰጣቸው ስብዕናዎች መካከል አንዱ ነው፡፡ ለሙስናና የስጦታ ድለላ ሳይታለል የእምነት ነጻነትን ጨምሮ ሙሉ ነጻነትና ጥገኝነትን ለነቢዩ ሙሐመድን(ሰ.ዐ.ወ) ባልደረቦች በመስጠቱና በኃላ ላይም ኢስላምን ተቀብሎ ኦክቶበር/ኖቬምበር 630 (ረጀብ ወር 9ኛ ዓ.ሂ.) ሲሞት የርሱን ሞት መልዓኩ ጂብሪል ሲነግራቸው ለርሱ ነቢዩ(ሰ.ዐ.ወ) ለሞቱ ሙስሊሞች ላይ የሚሰገደውን ሰላትን ሰግደዋል፡፡
(ኢማሙ ጦበሪ፣ ታሪኽ አል ሩሱል ወል ሙሉክ፣ ጥራዝ 3፣ ገጽ 81፤ ኢብኑ ከሲር፣ አል-ቢዳያ ወኒሃያ፣ ጥራዝ 3፣ ገጽ 99፤ ኢብኑል አሲር፣ አል-ካሚል ፊ ታሪኽ፣ ጥራዝ 1፣ ገጽ 347)
አላህም ንጉሥ ነጃሺ ኢስላምን መቀበሉን በማረጋገጥ የሚከተለውን የቁርኣን አንቀጽ አወረደ፡-
وَإِنَّ مِنْ أَهْلِ الْكِتَابِ لَمَنْ يُؤْمِنُ بِاللَّهِ وَمَا أُنْزِلَ إِلَيْكُمْ وَمَا أُنْزِلَ إِلَيْهِمْ خَاشِعِينَ لِلَّهِ لَا يَشْتَرُونَ بِآيَاتِ اللَّهِ ثَمَنًا قَلِيلًا أُولَئِكَ لَهُمْ أَجْرُهُمْ عِنْدَ رَبِّهِمْ إِنَّ اللَّهَ سَرِيعُ الْحِسَابِ (سورة : آل عمران آية: 199)
ከመጽሐፉ ሰዎች መካከል አላህን ፈሪዎች፣ በአላህ አናቅጽትም ጥቂትን ዋጋ የማይሸምቱ ሆነው በአላህ የሚያምኑ፣ ወደ እናንተ የተወረደውንም ወደነርሱ የተወረደውንም (እውነት የሚቀበሉ) ወገኖች በእርግጥ ይገኛሉ። እነርሱ ከጌታቸው ዘንድ (የላቀ) ምንዳ ተዘጋጅቶላቸዋል። አላህ ምርመራው ፈጣን ነው። (ቁርኣን፣ዓሊ ኢምራን፣ 3፡199)
(ይህ የቁርኣን ጥቅስ የወረደው በነጃሺ ምክንያት መሆኑን በርካታ የኢስላም ሊቃውንት በመጽሐፍቶቻቸው አብራርተዋል። ለምሳሌ፡- ኢብኑ ከሲር፣ ተፍሲር አል ቁርአን አል ዓዚም፣ ጥራዝ 3፣ ገጽ 199፤ ኢማሙ ጦበሪ፣ ጃሚዑል በያን፣ ጥራዝ 2፣ ገጽ 532፤ አል በገዊ፣ መዓሊም አት ተንዚል፣ ጥራዝ 2፣ ገጽ 155፤ ሲልሲለቱ ሶሒህ አል ሙኽተሰር፣ ጥራዝ 8፣ ገጽ 51፤ ኢብኑ ተይሚያህ፣ መጅሙዐቱል ፈታዋ፣ ጥራዝ 4፣ ገጽ 209፤ ተፍሲር ኢብን አቢ ሃቲም፣ ጥራዝ 3፣ ገጽ 318፤ አል-ሙዕጀም አል-አውሰጥ ሊ ጦበራኒ፣ ጥራዝ 10፣ ገጽ 357 እና ሌሎችም በርካታ መጻሕፍትን ማመልከት ይቻላል፡፡)
በዚህ ታሪኩና ማንነቱ የተነሳ የነጃሺ ስም በታሪክ ጎላ ብሎ ሰፍሯል፡፡
ዉቅሮ-ነጃሺ የሞተበት ስፍራ
📮📮📮📮📮📮📮📮
ዉቅሮ የሚገኘው የነጋሽ(ነጃሽ) ከተማ ደግሞ ንጉስ ነጃሺ የሞተበት ወይም የተገደለበት ስፍራ እንጂ የሕወሃት ሰዎች ሆነ ብለው ከአክሱምም ከነጃሺም ለመጠቀም ሲሉ እንደሰሩበት እና የመጅሊስ ሰዎችን ጨምሮ ብዙዎችም ልብ ሳይሉ እንደተከተሉት ነጃሺ መናገሻው ዉቅሮ ከተማ አልነበረም፡፡ የንጉስ ነጃሺ መናገሻ አክሱም ከተማ ነበር፡፡የነቢዩ ሙሐመድ(ሰ.ዐ.ወ) ሰሀቦች የእምነት ነጻነት ያገኙበትም አክሱም ራሷ ነበረች፡፡
በስደት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በአክሱም ከተማ ይኖሩ ከነበሩት መካከል በኃላ ላይ በንጉስ ነጃሺ ወኪልነት ለነቢዩ ሙሐመድ(ሰ.ዐ.ወ) የተዳረች ዑሙ ሀቢባ አንዷ ነበረች፡፡ ዑሙ ሀቢባና ሌላኛዋ የነቢዩ ሙሐመድ(ሰ.ዐ.ወ) ባልተቤት ኡሙ ሰለማና ኡሙ ሐቢባ (ረ.ዐ.) የአክሱም ማርያም (ጽዮን) ቤተ ክርስቲያንን ጎብኝተዋል።
በሶሂህ አል-ቡኻሪ የሐዲስ ጥራዝ ላይ በተዘገበው መሠረት በጉብኝታቸው ወቅት በቤተ ክርስቲያኒቱ የተመለከቱትን ‹‹የጻድቃን›› ምስሎች ወደ አገራቸው ከተመለሱ በኋላ ለነቢዩ ሙሐመድ (ሶ.ዐ.ወ) ነግረው ነበር። (Sahih Bukhari, Vol. 1, book 8, number 426 and Vol. 2, book 23, number 425)
እንደ የታሪክ ምሁር ፕሮፌሰር ስርግው ሐብለ ሥላሴ ገለጻ ስለአክሱም ጽዮን ቤተክርስቲን በስደት ወደ ኡሙ ሀቢባና ኡሙ ሰለማ ለነቢዩ ሙሐመድ(ሰ.ዐወ.) የገለጹበት ማስረጃ ስለቤተክሪስቲያኒቱ ዉስጣዊ ገለጻ "Elaborate and colorful description" (የተብራራና የሚያምር ገለጻ) ነው ያሉት።ፕሮፌሰር ስርግው "Ancient and Medieval Ethiopian History" በተሰኘው መጽሐፋቸው ገጽ 185 ላይ የግርጌ ማስታወሻ ቁጥር 30 ላይ ይህ አገላለጽ ቢያንስ ሁለት ጠቀሜታ እንዳለውና የአክሱም ጽዮን ቤተክርስቲያንን በተመለከተ የመጀመሪያው የታሪክ መረጃ መሆኑን አስረግጠው ጠቅሰዋል።
ታላቁ የቁርኣን ተንታኝ ኢማም ኢብኑ ከሲር ‹‹ተፍሲር አል-ቁርአኑል ዓዚም›› በተሰኘው የቁርኣን ማብራሪያ መጽሐፋቸው ላይ እንዳሰፈሩት ኢስላምን ከተቀበሉ በኋላ ንጉስ ነጃሺ ወደ ነቢዩ ሙሐመድ(ሰ.ዐ.ወ) ልከዋቸው የነበሩዋቸው የሀገራቸው ሰዎች ወደ ነጃሺ ተመልሰዋል። ስለ ነቢዩም (ሶ.ዐ.ወ) በዝርዝር ለነጃሺ ነግረዋል። ነጃሺ ኢስላምን ቀድሞ ቢቀበልም ከእነርሱ ከሰማ በኋላ ወደ ነቢዩ (ሶ.ዐ.ወ) ለመሄድ ጉዞ ጀምሮ ነበር። ግና ከአክሱም ከወጣ በኋላ በስደት (በጉዞ ላይ) በመንገድ ላይ ሞቷል።
(ተፍሲር አል-ቁርአኑል ዓዚም፣ ጥራዝ 3፣ ገጽ 166)
በኦክቶበር 2009 ትግራይ ውቅሮ ነጋሺ መንደር (ከመቀሌ ከተማ 65 ኪሎ ሜትር) በሄድኩበት ጊዜ የነጃሺን ቀብር ጎብኝቻለሁ። ከነጃሺ መቃብር በመቶዎች ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘው ቤተ ክርስቲያን ከነጃሺ ጋር የሚያገናኛት ታሪክ እንዳላት ሰማሁ።
በኦክቶበር 26/2009 ወደዚያው አቀናሁ። ‹‹ከዲህ ማርያም›› ቤተክርስቲያን ትሰኛለች። የቤተ ክርስቲያኒቱ ቄስ የ 75 ዓመቱ አዛውንት ቄስ ታደሰ ገብረ ሥላሴ በር ላይ ቆመው አገኘኋቸው። ስለ ቤተ ክርስቲያኒቱ ታሪክ ጠየቅኳቸው። ከስያሜው አመጣጥ ጀምረው እንዲህ ማብራራት ያዙ፡-
‹‹አንድ ሰው ወደ እስላም አገር ሊሄድ ሲል ከሚስቱ ጋር መጥቶ ነበር ይባላል። ከሚስቱ ጋር ሲሄድ ‹የት ነው የምንሄደው?› ብላ ሚስቱ ጠየቀች። ‹ወደ እስላም አገር እስልምናን ለማመን ነው የምንሄድ› ብሎ ተናገረ። ‹የት ነው የምንሄደው?› ብላ ለአሽከሮች ነገረች (ጠየቀች)፤ ‹ወደ እስልምና አገር፣ እስልምናን ለማመን ነው የምንሄድ ያለን› ብለው ነገሯት።
ከዚያ ወዲህ ‹አልሄድም› አለች፤ ቀረች። ከዚያ ባሏ ላይ (የአሁኑ የነጃሺ ቦታ) ሆኖ ጠይቋል። ‹ሚስቴ የት ሄደች?› አለ። ‹የለችም፤ አልመጣችም› አሉት። ‹ከዳች ወይ?› ብሎ ሲናገር ከዚያ በኋላ ነው እርሷ የነበረችበት ቦታ (ቤተ ክርስቲያኒቱ ያለችበት ቦታ) ከዲህ የተባለው ሲባል እንሰማለን። ከዚህ በኋላ (በመታሰቢያነት) ‹ከዲህ› ተብሎ ይጠራል።
ስለነጃሺ እንዲነግሩን ጠየቅኳቸው። ቦታውም እንዴት ‹‹ነጋሺ (ነጃሺ)›› ተብሎ እንደተሰየመም እንዲያብራሩልን ጠየቅኩኝ። ምላሻቸውን እንዲህ ሲሉ ቀጠሉ፡- ‹አይደለም። እኔ የምለው እኮ እርሱ ነው። ከሚስቱ ጋር የመጣው እርሱ ነጃሺ ነው። እርሱ ነጃሺ አደርእዝ ነው የሚባለው። እዚያ ላይ ነው ተገድሎ የሞተ ይባላል። በኋላ ነጋሺ ተብሎ ተጠራ። የርሱ ስም ነው። በንግሥና ስለመጣ ነው ነጋሺ እየተባለ የምንሰማው›› ብለው መለሱልኝ። ለተጨማሪ ጥያቄዎቼ ምላሻቸውን ቀጠሉ፡-
‹‹እርሱ ሚስቱንና አሽከሮቹን ይዞ በእስልምና ሊያምን ሲሄድ ሚስቱ ለአሽከሮቹ ጠየቀች። ‹የት ነው የምንሄድ?› ስትል፡፡ ‹ይህ ባልሽ ወደ እስልምና ለማመን ነው የሚሄደው› ብለው የነገሯት ጊዜ ‹እኔም ከዚህ አልሄድም› ብላ ከዚህ ቀረች።
እርሱም ላይ (የቀብሩ ቦታ) ነጋሺ በደረሰ ጊዜ ሌሎች ከአክሱም መጥተው ‹ወዴት ነው የሚሄደው?› ብለው ገድለውታል የሚባል ወሬ ነው የምንሰማው፡፡››
‹‹ንጉሥ ነበር?‹‹ ስል ጠየቅኳቸው። ‹‹አዎ!›› ሲሉም መለሱልኝ። ‹‹ሲሄድ ነው የተገደለው። ሊሄድ አይገባውም ብለው ነው፤ ‹ንጉሥ መስለም የለበትም› ብለው ነው ሲባል እንሰማለን…፤ እስላሞች ነጃሺ ይላሉ። እርሱ ግን አደርእዝ ነው። ‹ወደ እስልምና አገር ሄዶ ስማችንን ሊያጠፋ ነው› ብለው ገደሉት…›› ሲሉ መለሱልኝ።››
(አህመዲን ጀበል፣ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ከ615-1700 የጭቆናና የትግል ታሪክ፣2003፣ገጽ 53-54)
ሊዳፈን ያልቻለው የዉቅሮ የነጃሺ መካነ መቃብርና መስጊድ
🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥
የነጃሺ መቃብር አስጎብኚ እንዳብራሩልኝ በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት የነጃሺ መቃብር እንዳይታወቅ ይፈለግ ነበር። ቦታው እንዳይገነባ ማዕቀብ እንደተጣለበት፣ ሆኖም የዛሬ ሃምሳ ዓመት ገደማ (1946) የአድዋ ተወላጅና በወቅቱ አስመራ ይኖሩ የነበሩት ሐጂ ሙሐመድ ዐብዱ ኃይለ ሥላሴ ወደ ውጭ በሄዱበት በድብቅ በእምነበረድ አሠሩት።
ዛሬ የሐጂ ዐብዱ መቃብር በዚያው ግቢ ውስጥ ይገኛል። የንጉሥ ነጃሺ ሙሉ ስም ‹‹ዐፄ አደርእዝ አብሑር አብጀር›› እንደሆነም ገለፁልኝ።
የነጃሺና የተወሰኑ ሶሐባዎች መቃብር ላይ በግንብ ቤት ተሠርቷል። የነጃሺ መቃብር ከጥንት ጀምሮ በአካባቢው ይታወቃል። ለምሳሌ እ.ኤ.አ በ1533 ኢማም አሕመድ ኢብኑ ኢብራሂም አል-ጋዚ የአጋሜን ሹም ለማጥቃት በትግራይ በዘመቱበት ከነሠራዊታቸው የነጃሺን መቃብር ጎብኝተዋል። ዐረብ ፈቂህ ‹‹ፉቱህ አል-ሐበሻ›› በተሰኘው መጽሐፉ እንዲህ ጽፏል፡-
‹‹ከአሕመድ ነጃሺ ቀብር ዘንድ ደረሱ። የአላህ ራህመትና ሰላም ይውረድበትና እርሱ በነቢዩ ጊዜ የኖረው ነው። ‹ዛሬ ታዋቂውን አስሐማ አሕመድ አል-ነጃሺን እንዘይር። ነገ ደግሞ ወደ ትግሉ እንሄዳለን› ሲሉ ሙስሊሞች ኢማሙን (አሕመድን) ጠየቁ። ኢማሙ ‹ዛሬ በጣም አስፈላጊ (ጠቃሚ) በሆነ ዘመቻ ውስጥ ነን። ነገ እንጎብኝ› ሲል መለሰላቸው። ኢማም አሕመድ ከነፍሰጡር ባለቤታቸው ጋር በመሆን በውቅሮ የነጃሺን ቀብር ዘየሩ። የሙስሊሙ ጦርም የነጃሺን ቀብር ዘየረ። በዚያው ሳሉ የኢማሙ ሚስት ወንድ ልጅ ወለደች። የተወለደውን ልጅ (በኢትዮጵያዊው ሙስሊም መሪ ስም) ‹አሕመደል ነጃሺ›› ሲሉ ሰየሙት።››
(Shihab ad-Din Ahmad bin ‘Abd al-Qader bin Salem bin ’Utman ’Arab Faqih, Futuh al-Habaša. The Conquest of Abyssinia, Paul Lester Stenhouse (Trans.). USA. Tsehai Publishers and Distributors. 2003, Pp. 351-352)
አቶ ቡሽራ ሸኽ የህያ ‹‹የኢትዮጵያዊው ንጉሥ አሕመድ አል-ነጃሺ ታሪክ›› በተሰኘው መጽሐፋቸው ይህንን ጉዳይ አብራርተዋል። ጉዳዩ እንዲህ ነው፡-
አዝማች ሐጂ ሙሐመድ ዐብዱና ወንድሞቻቸው ለረጅም ዓመታት የንጉሡና የአስሓቦች መካነ መቃብርና መስጊዱ ዙሪያውን በድንጋይ፣ ጣራው በእንጨትና በአፈር ተሠርቶ የነበረው የተወሰነው ጎኑ እየፈራረሰ በማየታቸው ቅር ተሰኙ።
ቅርሱ ከጥፋት እንዲጠበቅና ለትውልድ እንዲተላለፍ በአዲስ መልክ ሊያስገነቡ ፈለጉ። የሥራ ፈቃድ ለማግኘት በ1945 ዓ.ል ወደ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ቤተ-መንግሥት አዲስ አበባ ድረስ ተጓዙ። የነጃሺን መቃብርና መስጊዱን ዳግም ሊያድሱ ፈቃድ ፈልገው መምጣታቸውን ለንጉሡ አማካሪ ለራስ እምሩ አማከሩ። ወደ ንጉሱ እንዲቀርቡ አደረጓቸው። ጥያቄያቸውን በጽሑፍ ለንጉሡ አቀረቡ።
ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ጉዳዩን ካደመጡ በኋላ ፈቃድ ከለከሉ። እነ አዝማች ሐጂ ሙሐመድ ዐብዱ አዝነው ወደ ትግራይ ተመለሱ። ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ፈቃድ ቢከለክሉም በኋላ ላይ የትግራይ ገዥ የነበሩት ራስ ሥዩም መንገሻ ‹በድብቅ ቀስ ብላችሁ ሥሩ› ብለው በመፍቀዳቸቸው ዳግም ታደሰ።››
(አቶ ቡሽራ ሸኽ የህያ፣ የኢትዮጵያዊው ንጉሥ አሕመድ አል-ነጃሺ ታሪክ፣ በድር ማተሚያ፣ መስከረም 2003፣ ገጽ 40-41)
ዐፄ ኃይለ ሥላሴም ወደ ግብጽ በአዝሐር ዩኒቨርሲቲ የነጃሺ መቃብር የት እንደሆነ ተጠይቀው በጭራሽ እንደማያውቁ ገልጸው ነበር። (ዐብደላ ዐብዱረሕማን ኑር፣ የዓይን ምሥክር፣ ገጽ 119)
በጥንታዊው የንጉስ ነጃሺና የሰሀቦች መካነ መቃብር ቅጥር ጊቢ ከጥንት ጀምሮ በነበረው የመስጂድ ፍርስራሽ ላይ በምስል የሚታወቀውን ዘመናዊ መስጊድ ያሰሩት ሼህ ሙሐመድ ሁሴን አላሙዲ ሲሆኑ የነጃሺን መንደርና ሙሉ ቅጥር ጊቢውን ዉብ በሆነ መልኩ ተመላልሰው ለምነው ያሰሩት ለታሪኩ ከፍተኛ ስፍራ የሚሰጡት ቱርኮች ነበሩ፡፡
በንጉስ ነጃሺ ስም በተለያዩ ሀገራት አደባባዮችና ተቋማት ሲሰየሙ ታሪኩና ቅርሱ ተገቢውን ስፍራ ባለማግኘቱ በሀገሩ በኢትዮጵያ ግን የሚገባውን ክብር አላገኘም፡፡ ስለነጃሺ መስጊድ መጠቃት መናገር ወይም መጻፍን አስመልክቶ በመቃወም ለመተቸት የሚሯሯጡትን ስታይ ‹‹የነጃሺ መስጊድስ የአክሱሙ ዱራ መስጊድ እጣ ፈንታ ይደርሰው ይሆን?›› አያስብልም?
ይቀጥላል…